Wednesday, July 31, 2013

ፍፁም አምባገነንነት

ፍፁም አምባገነንነት
ለሃያ ዓመት የቆየው ወያኔ አስተዳደርም የቀደሙ ታሪኮችን ከመድገም ባለፈ ጠብ ያደረገው አዲስ ነገር አለ ብሎ አፍን ሞልቶ መናገር አይቻልም፡፡ በተለይ በሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች አለመከበር ዙርያ፤ የፍትሕ ተቋማትን ተስፋ እንድንጥልባቸው ባለማድረግ ዙርያና ነፃ የሆነ የሚያኮራ ፕሬስ ባለመፍጠር ዙርያ የተሳካላቸው አይደሉም፡፡

‹‹ኢህአዴግ በተፈጥሮው ዴሞክራሲያዊ አይደለም›› የሚለውን ትችት እውነት እንደሆነ ለማረጋገጥ አይገደንም፡፡ እንደ ፖለቲካ አዋቂዎች አባባል ከሆነ ደግሞ የልግጥ ዲሞክራሲ ሲከተሉ የነበሩት ነፃ አውጪዎች 1997. በተካሄደው ሃገራዊ ምርጫ ላይ ያዩት የህዝብ ፍላጎትና ውጤቱ የልግጥ ዴሞክራሲውንም እርግፍ አደርገው በመተው ወደ ፍፁም አምባገነንነት(absolute dictator) የሚወስደውን ጎዳና አጥብቀው የያዙ ይሏቸዋል፡፡

ወያኔ ተከታዮቻቸው ወደ ፍፁም አምባገነንነት የሚወስደውን ጎዳና ሲይዙ እንደ አንድ ሞኝ ከመሬት ተነስተው ከዚህ በኋላ ምርጫ የለም፣ ተቃዋሚ አያስፈልግም፣ ነፃ ፕሬስ ማየት አንሻምብለው አልፎከሩም፡፡ ለምርጫ ተለጣፊ ተቃዋሚዎችን አበጁ፡፡ ለሃቀኛ ተቃዋሚዎችና ለነፃው ፕሬስ ደግሞ የህግ ሽፋን ለመስጠት ለምሳሌ የፀረ-ሽብር ህግ አዘጋጁ፡፡ የፀረ- ሽብርተኝነት ህጉ ተቀናቃኞችና ተቺ ጋዜጦችን ህግ እየጣሱ ለማሳደድ የሚመች ሆነላቸው፡፡ እና ኢህአዴግ ወደ ፍፁም አምባገነንነት እየተለወጠ ያለው ህግ እተጠቀሰ ነው፤ ተቃዋሚ አለ እያስባለና ነፃ ፕሬስ የትረፈረፈ እያስመሰለ ማለት ነው፡፡

ገዥዎች ሆይ! ዴሞክራሲያችንን ነጠቃችሁን ዝም አልን፣ ነፃነታችንን ጠቅልላችሁ ወሰዳችሁ ዝም አልን፣ የሚያስፈልጋችሁ ዳቦ እንጂ ሰብአዊ መብት ምናምን አይመለከታችሁም አላችሁን ዝም አልን፣ ግብር የምንከፍልበት የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንና አዲስ ዘመን ጋዜጣ የፓርቲ ልሳን እስከሚመስሉ የተቃዋሚዎች መርገሚያ አደረጋችኋቸው አሁንም ዝም አልን፣ ህዝብ ማወቅ የሚገባውን በመጨረሻም የመናገር ነጻነታችንን በአደባባይ ነጠቃችሁን እንግዲህ ምን ቀረን?
ከአንድናት ኢትዮጵያ ብሎግ


ኢትዮጵያ ክብር ለዘላለም ትኑር!

No comments: