Sunday, July 28, 2013

114 ኪሎ ሜትር የሐዲድ መስመር ለመዘርጋት ለባከነው 60 ሚሊዮን ዩሮ ተጠያቂው ማነው?


114 ኪሎ ሜትር የሐዲድ መስመር ለመዘርጋት ለባከነው 60 ሚሊዮን ዩሮ ተጠያቂው ማነው?

በአገራችን ለትራንስፖርቱ ዘርፍ ከፍተኛ ጠቀሜታ ሲሰጡ ከነበሩ አንጋፋና ታላላቅ ድርጅቶች መካከል የኢትዮ ጂቡቲ ምድር ባቡር ድርጅት አንዱና በሁለት እህትማማቾች አገሮችና (በኢትዮጵያና በጂቡቲ) ሕዝቦች መካከል ዲፕሎማሲያዊ ትስስሩ የማይበጠስ የጋራ መገናኛ ድርጅት እንደነበረ የቅርብ ጊዜ ትዝታችን ነው፡፡
ድርጅቱ ከዚህም ባሻገር ከአገራችን የሚወጡና ወደ አገራችን የሚገቡ ከፍተኛ ክብደት ያላቸውንና መጠነ ብዙ ለአገር ግንባታ የሚውሉ የፋብሪካ፣ የግብርና ወዘተ. ግባቶችን የሚያመላልስ ጠቃሚ የትራንስፖርት አካል ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር የመሀልና የዳር አገር ሕዝቦችም የኢኮኖሚ ጥምረት እንዲኖራቸው ያገዘና በርካታ ቤተሰቦችም እንዲተዳደሩበት ያደረገ እናት ድርጅት ነበር፡፡
ይሁንና ይህ ከአንድ ምዕተ ዓመት በላይ ዕድሜ ያለው ድርጅት በማርጀት፣ በጦርነት፣ በተፈጥሮና በአስተዳደራዊ ችግሮች ወዘተ. እንደቀድሞው ሊቀጥል ባለመቻሉ አንዳንድ ችግሮችን በተለይም በእርጅና የተበላሹ ሐዲዶችን (መስመሮች) መቀየር እንዲችል ከአውሮፓ ሕብረት (EU) የ60 ሚሊዮን ዩሮ ዕርዳታ ተሰጥቶት የ114 ኪሎ ሜትር መንገድ እድሳት እንዲደረግ ኮንስታ ጆይንት ቬንቸር ከተባለ የጣሊያን ድርጅት ጋር ውል ተደርጐ ሥራው ከአምስት ዓመታት በፊት እንዲጀመር መደረጉ ይታወቃል፡፡
ሆኖም ይህ የተባለው የኢጣሊያ ኩባንያ ከጅምሩ ለሥራው ብቁ እንዳልነበረ እየታወቀና በተለያዩ ጊዜያት ኃላፊነት ያለባቸው የምድር ባቡር የማኔጅመንት አባላት፣ የፋይናንስ ሚኒስቴር ተወካይ፣ የትራንስፖርት ሚኒስቴር ተወካይ እንደዚሁም ኮንሰልታንት የነበረው ኢኔኮ የተባለው ስፔናዊ ተቆጣጣሪ ድርጅት ጭምር ባልሳሳት በየጊዜው የተሠራውንና የተደረሰበትን ለመገምገም ድሬዳዋ እየተገናኙ ይነጋገሩ ነበር፡፡ ሆኖም ጠብ ያለ ሥራ ሳይሠራና 30 ኪሎ ሜትር ያህል እንኳን ሐዲድ ሳይዘረጋ ጠያቂም ተጠያቂም ሳይኖር ድርጅቱ (ኮንስታ) ከ1/3ኛ በላይ የሆነ ገንዘብ ካባከነ በኋላ የተጀመረው ሥራ እንዲቆም ተደርጓል፡፡
የሚገርመውና የሚያሳዝነው ደግሞ ምንም እንዳልተሠራና የመስመርና የድልድይ ሐዲዶች ተነስተው ለባሰ ኪሣራና ውድመት ድርጅቱ መዳረጉ እየታወቀ፣ ሕዝብና መንግሥትን ለማታለል መስመሩ እንደተሠራና እንዳለቀ ተቆጥሮ ባለፈው አምስት ወር ከፍተኛ ወጪ ወጥቶ ድል ያለ ድግስ ተደግሶ ምረቃ መደረጉ ነው፡፡ ለኮንስታም ድርጅት ሽልማት መስጠቱ እንደዚሁም በድርጅቱ ኃላፊዎችም የትራንስፖርት ሥራው ተጀምሮ በሳምንት አምስት ጊዜ ባቡር እየተመላለሰና ሥራው እንደተጀመረ መግለጫ መሰጠቱ አነጋጋሪ ነው፡፡
በያዝነው ወር ደግሞ የ114ቱ ኪሎ ሜትር 60 ሚሊዮን ዩሮና ለድግሱ ወጪ ብክነት ተጠያቂው ማን እንደሆነ ሳይለይ፣ ከድሬዳዋ ጂቡቲ መስመር ለማስቀጠል የድርጅቱ ኃላፊዎች ከፍተኛ ወጪ በማውጣት የሐዲድ መስመሩን ለመጠጋገን ዘመቻ ጀምረዋል (በቅርቡ አይሻ ላሠራውና ጐርፍ ወስዶት ተጠገነ የተባለውን 2,000,000 ብር ወጪ የሆነውን ሳይጨምር)፡፡ ሆኖም ግን ይሳካላቸው አይሳካላቸው ፈጣሪ የሚያውቀው ቢሆንም፣ ከ30 ዓመታት በላይ ድርጅቱን ሲመሩ የነበሩና ፈጽሞ ለኪሣራ የዳረጉ ሊጠየቁ ይገባል፡፡ በሐዲድ ሥራ ላይ (በባቡር ቴክኖሎጂ) ምንም ዓይነት ዕውቀት የሌላቸውና በሙስና የተጨመላለቁ የማኔጅመንት አባላት፣ ትላንት ድርጅቱ አነስተኛ ቢሆንም ለባቡሮችና ለጋሪዎች እንደዚሁም ለመስመር ሥራው ሐዲዶችና መለዋወጫዎች እያሉት ማስተዳደር ያልቻሉ፣ በቂ ባለሙያ በሌለበትና ሥራውን ለቆ በሄደበት ሁኔታ ዛሬ ከዜሮ ተነስቶ ምንም ሳይኖር ከድሬዳዋ ጂቡቲ ባቡር እንዲቀጥል እናደርጋለን ብሎ በድፍረት መነሳሳት፣ አገርን ለከፍተኛ ወጪ ሕዝብን ደግሞ ለአደጋ የሚዳርግ ነው፡፡ በመሆኑም ይህ በሰው ሕይወትና በንብረት ላይ መቀለድ ስለሆነ ሊታሰብበት እንደሚገባ ከወዲሁ መጠቆም እወዳለሁ፡፡
(ሜንታ ነኝ፣ ከድሬዳዋ)
************
የ15 ከተሞች መጠጥ ውኃና ሳኒቴሽን ፕሮጀክት ወቅታዊ ሁኔታ
የ15 ከተሞች መጠጥ ውኃና ሳኒቴሽን ፕሮጀክት በአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክና በአውሮፓ ኅብረት ብድርና ዕርዳታ በመካሄድ ላይ ያለ ፕሮጀክት ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ሦስት አካላት ያሉት ሲሆን፣ የፕሮጀክቱ አጠቃላይ ወጪ 36.2 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡ ይህም 16.5 ሚሊዮን ዩሮ ከአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ በብድር፣ 16.5 ሚሊዮን ዩሮ ከአውሮፓ ኅብረት በዕርዳታ የተገኘ ሲሆን፣ የተቀረውን ማለትም 3.2 ሚሊዮን ዩሮ በኢትዮጵያ መንግሥት የሚሸፈን ነው፡፡
ነገር ግን በጨረታ ወቅት በተለያዩ ምክንያቶች ዋጋ በመናሩ ምክንያት ፕሮጀክቱን ለማጠናቀቅ 50 ሚሊዮን ዩሮ በላይ እንደሚያስፈልግ ይገመታል፡፡ እ.ኤ.አ. ጥቅምት 23 ቀን በ2010 በተደረገው የጨረታ ሒደት የግንባታ ጨረታው ኮንስታ ስፓ ይመራው ከነበረው የሦስት ድርጅቶች ጥምረት ወይም ሽርክና ማቲዮሊ ጆይንት ቬንቸር በመባል ይጠሩ ከነበሩ የኮንትራክተር ስብስቦች ጋር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤታችን ውል በመፈራረም፣ ግንባታው እ.ኤ.አ. ጥር 20 ቀን በ2011 በይፋ ተጀምሮ ነበር፡፡
ሆኖም ኮንትራክተሩ በገባው ውል መሠረት ሥራ እንዲያጠናቅቅ የተሰጠውን ተደጋጋሚ ማሳሰቢያዎች፣ ትዕዛዞችና ማስጠንቀቂያዎች ላይ ትኩረት ባለመሰጠቱ ከድርጅቱ ጋር የነበሩንን ውሎች አስመልክቶ ከአበዳሪ፣ ከለጋሽ ድርጅቶቹና ከሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ጋር መወሰድ የሚገባውን ዕርምጃ አስመልክቶ ተደጋጋሚ ውይይቶችና ምክክሮች ከተደረጉ በኋላ፣ እ.ኤ.አ. ከየካቲት 12 ቀን 2013 ጀምሮ የግንባታ ውሉ እንዲቋረጥ ሆኗል፡፡
በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ አቋም መሠረት ይህ የውል መቋረጥ ቀደም ሲል መደረግ የነበረበት ቢሆንም፣ ከአውሮፓ ኅብረት የተገኘውን ዕርዳታ ላለማጣት ሲባል እንዲዘገይ ተደርጓል፡፡
ስለዚህ በቅርቡ የተከሰተው መቋረጥ የግንባታ ውሎቹ መቋረጥ ብቻ እንጂ ፕሮጀክቱ አለመቋረጡ ሊታወቅ ይገባዋል፡፡ ስለሆነም በዚህ ወቅት ከሁለቱ አበዳሪና ለጋሽ ድርጅቶች ጋር ያሉንን የብድርና ዕርዳታ ስምምነቶች ለማራዘም ከመግባባት ተደርሶ ጉዳዩ በሒደት ላይ ይገኛል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከሁለቱ አበዳሪና ለጋሽ ድርጅቶች በተደረገው ስምምነት መሠረት የተቀሩት ሥራዎችን ለማስጨረስ የጨረታ ሒደቱ እንዴት መሆን እንዳለበትና በምን መልኩ ሒደቱን ማሳጠር እንደሚቻል ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ተወያይቶ ከስምምነት ተደርሷል፡፡
በመሆኑም በቅርቡ በተቋረጡት ኮንትራክቶች ያልተቆፈሩ የውኃ ጉድጓዶች ለማስቆፈር ከአንድ ኢትዮጵያ ድርጅት ጋር የውል ስምምነት የተፈጸመ ሲሆን፣ የቧንቧና መገጣጠሚያዎች ግዢን ለማከናወን የጨረታ ሰነድ ዝግጅቱ በመጠናቀቅ ላይ ይገኛል፡፡ ስለሆነም የቧንቧና መገጣጠሚያዎች ግዢ ጨረታ በአጭር ቀናት ውስጥ እንደሚወጣ ይጠበቃል፡፡ የተቀሩት የሲቪልና የኤሌክትሮ ሜካኒካል ዕቃዎች ግዢና ተከላ የጨረታ ሰነዶች ዝግጅት በቅርቡ እንደሚጠናቀቅና አየር ላይ እንደሚውል እናረጋግጣለን፡፡ በሌላ ወገን የፕሮጀክቱ አካል የሆነው የአቅም ግንባታ ሥራ ውል ተፈጽሞ በአሁኑ ወቅት በተመረጡ ስምንት ከተሞች ሥራው ተጀምሯል፡፡
(የውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር)
የጥቂት ዳያስፖራዎችን ሕገወጥ ተግባር የሚመለከት ጥቆማ 
የኢትዮጵያ መንግሥት ከቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አቶ መለስ ዜናዊ ጀምሮ አሁን በሥልጣን ላይ እስከሚገኙ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ድረስ አገራችንን የበለፀገችና ለዜጎች ምቹ የሆነች አገር ለማድረግ ከፍተኛ ርብርብ እየተደረገ ነው፡፡ እኛም በትውልድ ኢትዮጵያዊ ሆነን በተለያየ አጋጣሚ የሌላ አገር ዜግነት ያለን ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ ባለን ዕውቀት፣ ገንዘብና ጉልበት የበኩላችንን ድርሻ እንድንወጣ ምቹ የሕግ ማዕቀፍ በማዘጋጀት ወደተግባር እንድንገባ ላደረጉትና እያደረጉት ላሉት በጎ ነገር ሁሉ ላመሰግን እወዳለሁ፡፡
አሁን ግን ይህን የመንግሥትና የሕዝብ ጥሪ እንደ ልዩ አጋጣሚ በመጠቀም በተለያዩ ተቀባይነት በሌላቸው ሥራዎች ላይ በመሳተፍ አገር እየጎዱ፣ የመንግሥትን ገቢ እያሳጡ እንዲሁም የብዙውን አገር ወዳድ ዳያስፖራ ልፋት መና እያስቀሩ በአቋራጭ ለመክበር የሚሯሯጡ ጥቂት ኪራይ ሰብሳቢ ዳያስፖራዎችን በቅርበት እየተመለከትን ነው፡፡
እነዚህ ዳያስፖራዎች ሕገወጥ ሥራዎችን በሕጋዊነት መጋረጃ በመጋረድ እያከናወኑ ይገኛሉ፡፡ ከሚፈጽሙትም ሕገወጥ ተግባሮች መካከል በውጭ አገር ያፈሩትን ጥቂት ሀብት የተለያዩ ውስብስብ መንገዶችን በመጠቀም አራጣ በማበደር በአጭር ጊዜ ለመክበር የሚያደርጉት ጥረት አንዱ ነው፡፡ ሌላው ደግሞ በተደጋጋሚ ከአገር ሲወጡና ተመልሰው ሲመጡ የግል መገልገያዎች በማስመሰል የተለያዩ ቁሳቁሶችን (በተለይ ኮምፒውተሮች፣ ኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችና የተለያዩ መድኃኒቶችን) አስፈላጊውን የመንግሥት ቀረጥ ሳይከፍሉ ይዘው በመግባት፣ ንግድ ፍቃድ ሳያወጡም ሆነ አስፈላጊውን መንገድ ሳይከተሉ ለገበያ እያቀረቡ ሕጋዊ ነጋዴውን እየጎዱ ይገኛሉ፡፡
በዚህ አጋጣሚ ለትውልደ ኢትዮጵያውያን አስፈላጊውን ፍቃድና መታወቂያ እንዲሰጥ ኃላፊነት የተሰጠው የመንግሥት አካል፣ አዲስ ፈቃድ ሲሰጥም ሆነ የነበረውን ሲያድስ አገር ውስጥ በምን ሥራ ላይ ለመሳተፍ እንዳሰቡና እየተሳተፉ እንደሚገኙ የማጣራት ሥራ ቢሠራ መልካም ነው፡፡ እንዲሁም የፍትሕ አካላትና የገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን አስፈላጊውን ክትትል ቢያደርጉ፣ ይህንን ሕገወጥ ተግባር ሥር ከመስደዱ በፊት ለመግታታት እንደሚቻል አምናለሁ፡፡
ከሁሉ ሁሉ በላይ ግን የአገራችን ልማት የሚናፍቀን ኢትዮጵያውያን ሆንን ትውልደ ኢትዮጵያውያን እነዚህን ጥቂት ሕገወጦች ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ በቃችሁ በማለት ከመምከር ጀምሮ አስፈላጊውን ጥቆማ ለተገቢው አካል መስጠት ይገባል፡፡ ይህንንም ከማድረግ እነዚህ ግለሰቦች ከሕገወጥ ተግባራቸው ተገትተው ራሳቸውንም ሆነ አገርን በሚጠቅም ተግባር እንዲሳተፉ በማድረግ ለተነሳንለት ራዕይ የበኩላችንን ኃላፊነት እንድንወጣ እጠይቃለሁ፡፡
(የአገርን ጥቅም ከሚያስቀድሙ ትውልደ ኢትዮጵያውያን አንዱ)
ethiopian reporter

No comments: