Wednesday, August 21, 2013

በሙስሊሙ መካከል የልዩነት እሳት?

በሙስሊሙ መካከል የልዩነት እሳት?
ረቡእ ነሐሴ 15/2005

በጣም ግልጽ በሆነ መልኩ ከሰሞኑ የመንግስት ፕሮፖጋንዳዎች መረዳት የቻልነው እውነታ መንግስት ሙስሊሞችን ከሌሎች እምነት ተከታዮች ጋር ብቻ ሳይሆን እርስ በእርሳችንም የተለያዩ ስያሜዎች ተሰጣጥተን እንድንጫረስ ያለመ መሆኑን ነው፡፡ እንደሚታወቀው በሙስሊም ምሁራን መካከል የነበሩ አንዳንድ የሃሳብ ልዩነቶችን ለመፍታት ከፍተኛና ተከታታይ ውይይቶች ሲካሄዱ መቆየታቸው ይታወሳል፡፡ በእነዚህ ውይይቶች ተቀዳሚ ሙፍቲ ሐጂ ኡመር እድሪስና ዶ/ር ጄይላንን ባካተተ መልኩ ለወራት ሲደረግ ቆይቶ በመሰረታዊ ሐሳቦች ላይ ስምምነት በመደረሱ አጠቃላይ የውህደት ፕሮግራም ለመፈጸምና የመግባቢያ ሰነድ ለመፈረም ዝግጅት በተደረገበት ወቅት ነው የመንግስት አካላት ውይይቱም ሆነ የአንድነት ፕሮግራሙ እንዲገታ በማድረግ የተጀመረውን አስደናቂ ሂደት እንዲደናቀፍ ያደረጉት፡፡ በዚህ ሂደት ዋነኛ ተዋናይ የነበሩት የአህመዲን አብዲላሂ ጨሎ መጅሊስ አባላት ሲሆኑ ከፍተኛ የደህንነት ሐላፊዎች የውይይቱን አስተባባሪዎች እነ ሐጂ ኡመር እድሪስን በማስፈራራት እና ዛቻ በመሰንዘር ከተቀደሰ ተግባራቸው እንዲታቀቡ አድርገዋቸዋል፡፡ ሐጂ ኡመር እድሪስ በአንድነት ፕሮግራሙ በመሳተፋቸው ብቻም በመጅሊሱ ውስጥ በወቅቱ የነበራቸውን ስልጣን እስከመቀማት ደርሰዋል፡፡ የአንድነት ፕሮግራሙ ፍጻሜ አግኝቶ ቢሆን ኑሮ የመንግስታዊ ሃይማኖት አመራሮቹ ሊፈነጩበትም ሆነ ጸረ አንድነት አጀንዳቸውን ሊረጩ የሚችሉበት ቦታ ማግኘት ይሳናቸው እንደነበር ግልጽ ነው፡፡ መንግስትም በሙስሊሙ አንድነት የሚመጣውን ለውጥ ቀድሞ በመገንዘብ ይህንኑ በር ለመዝጋት ይህ ነው የማይባል ጥረት አደረገ፡፡

ይህን ሁኔታ ማስታወስ ብቻ የመንግስትን ፍላጎትና ግብ ለመረዳት በቂ ነው፡፡ መንግስት አሁን ሊያስተላልፍ እየፈለገ ያለው መልእክት ‹‹የነካሁት የተወሰኑ ሙስሊሞችን እንጂ ሌሎች ሙስሊሞችን አይደለም፤ እገሌ የተባለውን ቡድን እያጠቃሁ በመሆኑ ሌሎቻችሁ አግዙኝ›› መሆኑ ነው እንግዲህ፡፡ መንግስት መሰረታዊ ስህተት የሰራው እዚህ ላይ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች መንግስት እንደሚለው እርስ በእርስ ስያሜ ተሰጣጥተን በልዩነት የምንዳክርበት ጊዜ ፈጽሞ እንደሌለ እሙን ነው፡፡ በመሰረቱ መንግስት ‹‹አክራሪነትን እዋጋለሁ›› በሚል ሰበብ ጦሩን መዞ የሚገኘው ሙስሊሙ ላይ መሆኑ ለአፍታ እንኳ ጥርጣሬ ተሰምቶን አያውቅም፡፡ ይህን ለመረዳት መንግስት ለፖለቲካ አመራሮቹ በ2003 እና በ2004 አዘጋጅቷቸው የነበሩ ሰነዶችን መመልከቱ በቂ ነው፡፡ ከዚህ በፊት በስፋት ሲገለጽ እንደነበረውም በእነዚህ ሰነዶች መንግስት ሃይማኖታዊ ተግባራትን መፈጸም ሁሉ አክራሪነትና አሸባሪነት እንደሆነ አስፍሯል፡፡ መንግስት በለበጣ ስያሜ እየሰጠ አንዱን ሙስሊም በሌላው ላይ ለማስነሳት በቴሌቪዥን ፕሮግራሙ ዘፈን እስከማዘፈን ደርሷል፡፡ ይህ ጅምር ነገ ምን ይዞ ሊመጣ እንደሚችል ጥያቄ የለውም፡፡ ‹‹እገሌ የሚባለው ቡድን ተነስቶብሃልና ታገለው!›› የሚል መልእክት በማስተላለፍ አንዱን ጨርሶ ወደ አንዱ መሄድ የመንግስት የተለመደና ያረጀ ያፈጀ ስልት ነው፡፡

በሙስሊሙ መሀከል የልዩነት እሳት ማንደድ የድሮው መጅሊስ ሲሞክረው የቆየ ቢሆንም የተሳካለት ግን በጣም ጥቂት ነው፡፡ አሁን አልሀምዱሊላህ ሙስሊሙ ኡምማ አንድ ነው፡፡ ራሱን በተለያዩ ስያሜዎች ከፋፍሎ እርስ በእርሱ የሚናቆርበት መንገድ አይኖርም፡፡ መንግስት ሙስሊሙ ላይ የሰነዘረው ጥቃት ለሙስሊሙ አንድ መሆን ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክቷል፡፡ ሙስሊሙ ህብረተሰብ ከመንግስት የተሰነዘረበትን ቡጢ እየመከተም እየተሸከመም ያለው በጋራ ያለ ምንም ልዩነት ነው፡፡ ‹‹አዲሱ›› እና ‹‹አሮጌው›› የሚባል እስልምና የለም፡፡ ‹‹ነባሩ›› እና ‹‹መጤው›› የሚባል የስያሜ ልዩነት በመካከላችን የለም፡፡ ይህን በአፍ ብቻ ሳይሆን በተግባርም ጭምር ሙስሊሙ አረጋግጧል፡፡ ተቃውሞ እያካሄደ ያለው መላው ሙስሊም ህብረተሰብ እንጂ የተወሰነ አስተሳሰብ ያለው አካል እንዳልሆነ በተለያዩ ክፍለ ሃገራት የተደረጉት የአንድነትና የሰደቃ ፕሮግራሞች አሳይተዋል፡፡ በተግባር የታየው አንድነትና አብሮ መፋቀር መንግስትን አስደንግጦታል፡፡ መሪዎቻችን የሰሩት ጀብዱ ሙስሊሙን ሁሉ በአንድ ጥላ ስር መሰብሰባቸው፣ በአገር አቀፍ ደረጃ አንድ አይነት ስሜት እና ውህደት መፍጠራቸው ነው፡፡ ይህ አንድነት በመንግስት ሴራ ፈጽሞ ሊገረሰስ አይችልም!
ድምፃችን ይሰማ

No comments: