Friday, December 25, 2015

በአካል ሊጎዱት ይችላሉ ወኔውን እና መንፈሱን ግን አይነኩትም - ግርማ ካሳ



አገር ቤት ካሉ ከማደንቃችው አንጋፋ የዲሞክራሲ ተሙዋጋቾች መካከል አንዱ ጌታቸው ሽፈራው ነው። ጋዜጠኛ ነው። በእጁ ያለው ብእርና ኪቦርድ ነው። ግን ሀሳብን በሐሳብ መመከት 
የማይችሉ፣ የጫካ አስተሳሰብ ያለቀቃቸው ደካሞች አፍነው ወደ ወህኒ ወሰዱት።
ጌታቸውን እናዉቀዋለን። ድብቅ ነገር አያውቅም። የሚጽፈዉን፣ የሚጦምረውን አገር ሁሉ፣ ሕዝብ ሁሉ ነው የሚያነበው። ሆኖም የጌታቸው ቃላት ለደካሞች ራስ ምታት ሆነባቸው።
ጌታቸው ሳይፈራ ሲጽፍ፣ ሲጦምር ሊታሰር፣ ሊገደል እንደሚችል ያውቀዋል። ሆኖም "ሰው ያለነጻነቱ ምንድን ነው ?" እንደተባለ፣ ያለ ነጻነት መኖር አለመኖር መሆኑን በመረዳቱ መኖርን መረጠ። ለአገርና ለህዝብ ፍቅር ስላለው "ስለሚያገባኝ እጦምራለሁ፤ ስለሚያገባኝ እጽፋለሁ" ብሎ ጦመረ፣ ጻፈ።
አላወቁትም እንጂ ወያኔዎች ጌታቸውን ወደ ወህኒ ቢወስዱትም፣ እርሱ ግን ለአገር መታሰርን እንደክብር ነው የሚቆጥረው። አካሉ ላይ ጉዳት ሊያደርሱ ይችላሉ እንጂ በምንም መልኩ ወኔው፣ መንፈሱን፣ ዉስጡን ሊነኩ አይችሉም።
ጌታቸው ሽፈራው ለታሰሩ ወገኖች ትልቅ ሸክም የሚሰማው ሰው ነው። በወጣት በላይ ማናዬ ጋር በሚያዘጋጁት ዝነኛዋ የአዲስ ነገር ጋዜጣ፣ በየጊዜው የእስረኞችን የፍርድ ሂደት እየተከታተለ ለህዝብ ሲያቀርብ የነበረ ወጣት ነው። እስረኞች ተሙዋጋች የሆነ ወንድም እርሱም እስረኞችን ተቀላቀለ።
እነጌታቸውን በማሰር የነጻነትን ድምጽ አፍናለው ብለው ወያኔዎች አስበው ከሆነ ራሳቸውን ነው የሚያታልሉት። አሁን ትግሉ የሚሊዮኖች ነው። ሚሊዮኖችን ማሰር አይችሉም።


No comments: