Friday, December 18, 2015

መንገድ ሲዘጋ የኖረው ህወሃት/ኢህአዴግ መንገድ እየተዘጋበት ነው

"ሕዝቡን ተንገሽግሾዋል"
thursday

ላለፉት ሦስት ሳምንታት የኦሮሞ ብሔረሰብ አባላት ተማሪዎች የአዲስ አበባ እና የፊንፊኔ ዙሪያ የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ ማስተር ፕላን ተግባራዊ ይደረጋል መባሉን ሲቃወሙ ሰንብተዋል። የተቃውሞውን ጅምር የሚያትተውን የማርታ ፋን ደር ቮልፍ የአዲስ አበባ ዘገባ ጨምራ፤ ጽዮን ግርማ የዛሬዉን የተቃውሞ ሰልፍ ውሎ የተመለከት ርእሶችን ይዛለች፡፡ (የዜና ዘገባው ያሜሪካ ድምጽ ሬዲዮ ነው)
የተቃውሞው መነሻ  “ያለ ተገቢ የገንዘብ ክፍያ ገበሬዎችን የሚያፈናቅል የመሬት ቅርምት ነዉ” የሚል መኾኑ ሲዘገብ ቆይቷል። የጸጥታ ኃይሎች ሰልፈኞቹ ላይ በወሰዱት ርምጃ ቢያንስ አምስት ሰዎች እንደተገደሉ መንግሥት  አምኗል። የተቃዋሚ ድርጅት መሪዎች በበኩላቸው የተገደለዉ ሰዉ ቁጥር ስልሳ እንደሚደርስ ተናግረዋል፡፡ የጸጥታ አስከባሪዎች ሕይወት ማለፉም ተገልጿል።
የኦሮምኛ ቋንቋ ዝግጅት ክፍል ባልደረቦቻችን ስለ ዛሬው  የተቃውሞ ሰልፍ ውሎ ምንጮቻቸውን ጠቅሰው እንደዘገቡት፤በዛሬው ዕለት በምዕራብና ምስራቅ ወለጋ፣ በሱሉልታ፣ በሆሮ ጉድሩ፣ በነጆ፣ በጫንቃና በሌሎች ቦታዎች  ሰልፉ መቀጠሉንና በዚሕም የሰው ሕይወት መጥፋቱ ተገልጿል፡፡
በሌላ በኩል በኢሉባቡር አልጌ ሳቺ ከተማ ለሰላማዊ ሰልፍ የወጡ ሰዎች ተቃውሟቸውን አሰምተው በሰላም መመለሳቸው ታውቋል፡፡ በተጨማሪም ቁጥራቸው ያልታወቁ ሰዎች መታሰራቸውን አብዛኞቹ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች በፌደራልና መከላከያ ፖሊስ ጥብቅ ጥበቃ ሥር መዋላቸውን ዘግበዋል፡፡thur
በሌላ በኩል ማርታ ከአዲስ አበባ ባጠናከረችው ዘገባ  “የተማሪዎቹ ተቃውሞ ወዲያዉ በአዲስ አበባ ከተማ ዙሪያ ያሉ የኦሮሚያ ክልልን አዳረሰ፡፡” ሲል ይጀምራል፡፡ ገበሬዎችና ሌሎች ነዋሪዎችም በተቃውሞዉ ተማሪዎቹን ተቀላቀሉ። መንግሥት አንዳንዶቹ ተቃዋሚዎች አገሪቱን ለማናጋት የሚንቀሳቀሱ ናቸዉ በማለት ይከሳል። ለደህንነታቸዉ በመስጋት ስማቸዉ እንዳይጠቀስ የጠየቁ አንድ የክልሉ ነዋሪ፤ ወደ ክልሉ የተላኩ የጸጥታ ኃይሎች ሌሎች ሰዎች ተቃውሞውን እንዳይቀላቀሉ መንገዶችን ዘግቶ እየተቆጣጠረ እንደኾነ ተናግረዋል።
እንደ ነዋሪው ገለፃ “አብዛኞቹ ተቃዋሚዎች ገበሬዎች ናቸዉ። ከገጠር አካባቢዎች ነው ወደ ከተሞች የሚመጡት። የመከላከያ ኃይል ደግሞ ወደ እነዚህ ገጠሮች አምርቷል። ፖሊሶችም ተቃዋሚ ሰልፈኞቹን ቁጥጥር ስር እያዋሉ ነዉ።”
የኢትዮጵያ መንግሥት ተቃዋሚ ሰልፈኞቹ ከጸጥታ አስከባሪዎች ጋር ባደረጉት ግጭት አምስት  ሰዎች መሞታቸዉን አረጋግጫለሁ ብሏል፣ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ግን የተገደሉ ሰዎች ቁጥር 60 ደርሷል ይላሉ። ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅት አምነስቲ ኢንተርናሽል (Amnesty International)  ትላንት ዕረቡ ባወጣዉ መግለጫ መንግሥት ተቃውሞዉን በኃይል እያፈነ ነዉ ብሏል።
በአዲስ አበባና ዙሪያዋ የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ ማስተር ፕላን የተባለውን በመቃወም ባለፈዉ ዓመት ሚያዚያ ወርም እንዲሁ ተቃውሞ ተነስቶ ነበር። ተቃውሞዉን ተከትሎ የጸጥታ ኃይሎች በወሰዱት የኃይል ርምጃ በደርዘኖች የሚቆጠሩ ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል፡፡ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸዉ ሰዎችም ታስረዋል። ማስተር ፕላን የተባለዉ የዋና ከተማዋን ማለትም የአዲስ አበባን ድንበር የሚያሰፋ ንድፍ ነዉ። በዙሪያዋ የሚኖሩ የኦሮሚያ ክልላዊ አስተዳደር ዜጎች “የታቀደው መዋቅር መሬታችንን ነጥቆን የባህል ቅርሶቻችንን የሚያወድም በመኾኑ ያሳስበናል” ይላሉ።
thuየኢትዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናት ካለፈዉ ዓመት ተቃውሞ በኋላ ስለ ማስተር ፕላኑ ጉዳይ ከሚመለከታቸዉ አካላት ጋር ሁለገብ ዉይይት ለማድረግ ቃል ገብተው ነበር። ተቃዋሚው የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ መሪ ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና እነዚያ ቃል የተገቡት ውይይቶች አልተደረጉም ይላሉ።
“ብዙ ጊዜ ውይይት እንዲደረግ ሞከርን፣ አናደርግም አሉ። ከዚያም ግልጽ ሕዝባዊ ስብሰባ ለማድረግ ሞከርን እሱንም እንቢ አሉ። መንገዱን ዘጉብን። አሁን እንግዲህ እዚህ ላይ ደረስን። የዚህ መንግሥት ሁኔታ ሕዝቡን አንገሽግሾታል። በተለይም ወጣቱ ይህ መንግሥት በሚያደርገው ነገር ኹሉ ተንገሽግሿል።”ሲሉ ይገልጻሉ፡:
ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ፤ “ማስተር ፕላኑ መሰረዝ አለበት፡፡ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥትም ፈርሶ በሌላ መተካት አለበት” ይላሉ። መንግሥት በበኩሉ ማስተር ፕላኑ ሥራ ላይ አልዋለም ይላል፤ ተቃዋሚዎች ደግሞ ገበሬዎችን ማፈናቀል ከተጀመረ እንደቆየ ይገልጻሉ።
በኢትዮጵያ ብዙም ተቃውሞ አይካሄድም። ገዢዉ ፓርቲ እንደ አዉሮፓውያን አቆጣጠር በ1991 ዓ.ም ሥልጣን የያዘ ሲኾን ባለፈው ግንቦት ወር በተካሄደ ምርጫ ሙሉውን የምክር ቤት መቀመጫ ተቆጣጥሯል። የጸጥታ ጥናቶች ተቋም ባልደረባ ሃሌሉያ ሉሌ ውጥረት እንደሰፈነ ይናገራል።
“ታይቶ የማይታወቅ ከፍተኛ ተቃውሞ እየተመለከትን ነዉ። የጸጥታ ኃይሎቹም ኾነ መንግሥት የተከሰተዉን ከፍተኛ ተቃውሞ የጠበቁ አይመስለኝም። በእኔ እምነት የክልሉ መንግሥትም እንዲህ ዓይነቱን ጥያቄ ለመመለስ የተዘጋጀ ያለመኾኑን ሁኔታዉ አሳይቷል”ብሏል፡፡
ሙሉ ዘገባውን ከተያያዘው ድምጽ እዚህ ላይ ያድምጡ፡፡
በሌላ በኩል ሳምንታት ያስቆጠረው ህዝባዊ ንቅናቄ ሃሙስም ቀጥሎ ውሎዋል፡፡ በሰላማዊ ትግል አሠራር መሠረት በተለይ በሱሉልታና ሌሎች አካባቢዎች የታየው ስልት የትግሉን መስመር መያዝ እንደሚያሳይ ተጠቁሞዋል፡፡ ሱሉልታ ለአዲስ አበባ ከመቅረቡዋ አኩዋያ ነዋሪዎች የመኪና መንገዱን ዘግተው መዋላቸው ያደረሰው ተጽዕኖ በአገዛዙ በኩል ሄሊኮፕተር እስከማሰማራት ያደረሰ ሆኖዋል፡፡
የዘር ጽንፈኝነትን የሚቃወሙ ወገኖች ንቅናቄው ሁሉን አቀፍ እንዲሆን ጥሪ እያደረጉ ሲሆን በህወሃት/ኢህአዴግ አገዛዝ በኩል ደግሞ ንቅናቄውን ለማኮላሸት የዘር ልዩነቶችን ማስፋትና ከተቻለም መጎዳዳት እንዲከሰት የማድረግ ሥራዎች ይሠራሉ የሚሉ ወገኖች ህዝቡ ይህንን ከመሰለ የዘርና የሃይማኖት ክፍፍል እንዲቆጠብን ያሳስባሉ፡፡
ሕዝባዊ ንቅናቄው ይህንን ያህል ሳምንታት መቆየት መቻሉ እጅግ አሳሳቢ ሲሆን በህወሃት/ኢህአዴግ በኩል የሚፈጸመው ግድያ አሁንም ቀጥሎ እስካሁን የሞቱት ከመቶ በላይ እንደሆኑ በተለያዩ የማኅበራዊ ሚዲያዎች ይነገራል፡፡ 
Source: ጎልጉል

No comments: