Tuesday, June 14, 2016

የሀገር መከላከያ ሚኒስቴር ወታደሮችን ለመቅጠር ማስታወቂያ ቢያወጣም የሚመዘገብ ወጣት ሊያገኝ አለመቻሉ ተገለጸ።

ሰኔ (ሰባት) ቀን ፳፻፰ / ኢሳት ዜና :-በወታደርነት መቀጠር የሚፈልጉ 18 ዓመት በላይ የሆኑ  ወጣቶች   ከግንቦት 30 እስከ ሰኔ 10 ቀን 2008 ዓመተ ምህረት ድረስ እንዲመዘገቡ የሚጠይቁ ማስታወቂያዎች በየቦታው ቢለጠፉም የሚመዘገቡ ወጣቶች ቁጥር አነስተኛ መሆን ገዢው ፓርቲን አሳስቦታል።
በማስታወቂያው ከወጡት መስፈርቶች መካከል ኪሎ- 50 እስከ 70 የሆነ፣ ቁመት 1 ሜትር 60 በላይ በብሔረሰብ እኩልነት የሚያምንና ከዚህ ቀደም ፖሊስ ወይም ወታደር ሆኖ የማያውቅ የሚሉት ይገኙበታል። ሰሞኑን የአልሸባብ ታጣቂዎች  በሶማሊያ  ተልዕኮ ላይ የነበሩ በርካታ የኢትዮጵያ  ወታደሮችን መግደላቸውን ተከትሎ  መረበሽ ወስጥ የገባው የህወኃት ኢህአዴግ መንግስት  በኤርትራ ላይ  የትንኮሳ ሙከራ ማድረጉ በመገናኛ ብዙሃን ሲዘገብ ቆይቷል።
ኢህአዴግ- በኤርትራ ላይ ጦርነት የሚከፍተው ለሉዓላዊነት  ብሎ ሳይሆን በኤርትራ ያሉ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎችን ለመውጋትና የራሱን የሥልጣን ዕድሜ ለማራዘም ስለሆነ ሀገሩንና ነጻነቱን  የሚወድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ በዚህ ከንቱ ጦርነት እንዳይማገድ አርበኞች ግንቦት ሰባት ባወጣው መግለጫ ማሣሰቡ ይታወሳል። ውድ ተመልካቾቻችን አልሸባብ ሰሞኑን ባደረሰው ጥቃትና በሶማሊያ ስላለው ሁኔታ ሚስጢራዊ መረጃ በነገው ዘገባ የምናቀርብ መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን።

No comments: