Tuesday, June 21, 2016

የኢትዮጵያ መንግስት ያለበት እዳ 36.6 ቢሊዮን ዶላር መድረሱ ተገለጸ

የኢትዮጵያ መንግስት እስከ ፈረንጆች አቆጣጠር 2015 ዓም ማጠናቀቂያ ድረስ ያለበት አጠቃላይ እዳ 36.6 ቢሊዮን ዶላር መድረሱ ተገለጠ።
ይኸው የሃገሪቱ የእዳ መጠን ከአጠቃላይ ሃገራዊ ምርት ጋር ሲነጻጸር ወደ 55 በመቶ የሚደርስ ሲሆን፣ መንግስት ከሚያጸድቀው በጀት ውስጥ ለእዳ ክፍያ የሚመደበው ገንዘብ እየጨመረ መምጣቱ ታውቋል።
2009 ዓም ከተያዘው 274 ቢሊዮን ብር በጀት መካከል መንግስት ወደ 14 ቢሊዮን ለእዳ ክፍያ መመደቡ ይታወሳል።
እንደፈረንጆቹ አቆጣጠር 2014/2015 ዓም የኢትዮጵያ አጠቃላይ በጀት ወደ 19 ቢሊዮን ዶላር ደርሶ የነበረ ሲሆን፣ ብድሩ በከፍተኛ ሁኔታ ጭማሪን በማሳየት በአሁኑ ወቅት 36.3 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን በሃገር ውስጥ ያሉ መገናኛ ብዙሃን የገንዘብና የኢኮኖሚ ሚኒስቴር መረጃን ዋቢ በማድረግ ዘግበዋል።
የኢትዮጵያ ውጭ እዳ መጠን ብቻ ወደ 20 ቢሊዮን ዶላር አካባቢ መሆኑንና የእዳ መጠኑ የሃገሪቱ አጠቃላይ አመታዊ ምርት 30 በመቶ እንደሚሸፍን ታውቋል።
ለብድር የሚከፈለው የወሊድ መጠን ከፍተኛ መሆኑን የገልጹት የምጣኔ ሃብት ባለሙያዎች በበኩላቸው የሃገሪቱ አጠቃላይ እዳ እየጨመረ መምጣት በኢኮኖሚ እድገቱ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖን ማሳደሩን አስረድተዋል።
በተያዘው 2008 አም ብቻ መንግስት ከአለም ባንክ የተበደረው እዳ 1.8 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን፣ የቻይና መንግስትን ጨምሮ የተለያዩ አበዳሪ አካላት ከፍተኛ ገንዘብ በብድር ማቅረባቸው ታውቋል።
የአለም ባንክ በተያዘው በጀት አመት ለኢትዮጵያ ያበደረው ገንዘብ ከዚህ በፊት ከነበሩ ብድሮች ጋር ሲነጻጸር በመጠን ከፍተኛው ሆኖ ተመዝቧል።
ሃገሪቱ የምትበደረው ገንዘብ በመጨመር ላይ ቢሆንም ከውጭ ንግድ የሚገኘው የውጭ ምንዛሪና ክምችትን ግን እየቀነሰ መምጣቱን የንግድ ሚኒስቴር በቅርቡ ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።
የኢትዮጵያ መንግስት ያለበት የእዳ ክምችት እስከ 30 አመት በሚደርስ ጊዜ የሚጠናቀቅ በመሆኑ ሃገሪቱ በወለድ የምትከፍለው ገዘብ መጠን ከፍተኛ መሆኑ ይነገራል።
ኢሳት


No comments: