Monday, August 8, 2016

ከማረሚያ ቤት እየቀረቡ ሲከራከሩ የከረሙ ተከሳሾች በብይን የሉም በመባላቸው ዳኞችን ከሰሱ

ከአንድ ዓመት በላይ ከፌዴራል ማረሚያ ቤት እየቀረቡ ሲከራከሩ የከረሙ የኢትዮጵያና የውጭ አገር ዜጎች ጉዳያቸውን ሲመረምር የከረመው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሦስተኛ ወንጀል ችሎት ሰኔ 23 ቀን 2008 ዓ.ም. ብይን ሲሰጥ ‹‹ተከሳሾቹ በችሎት ስላልቀረቡ ክሱ ተቋርጧል›› ማለቱን ተከትሎ ተከሳሾቹ የችሎቱ ሦስት ዳኞች ላይ አቤቱታ አቀረቡ፡፡
ከማረሚያ ቤት እየቀረቡ ሲከራከሩ ቆይተው በሌሉበት ክሱ መታየት ስለማይችል ክሱ እንደተቋረጠ ተደርጎ ብይን መስጠቱ አግባብ አለመሆኑን በመግለጽ ለፌዴራል ዳኞች አስተዳደር ጉባዔ አቤቱታ ያቀረቡት ተሸሳሾች፣ ኢትዮጵያዊው አሽራፍ አወልና የሲሪላንካ ዜጎች መሆናቸው የተገለጸው ሚስተር ሒትራጂግ ያሳንታ፣ ሚስተር ፕላን ዋታጅ አሲታ፣ ሚስተር ቦፒ ጊድራ አጅትና ሚስተር ኩሩፑ ኢራችግ ዶን ናቸው፡፡
ተከሳሾቹ እንደገለጹት ለጳጉሜ 5 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ ዋስትና ተከልክለው ከማረሚያ ቤት እየተመላለሱ ጉዳያቸውን እየተከታሉ ናቸው፡፡ በብይኑ በሌሉበት ክሳቸው የሚታይ ስላልሆነ ክሱ እንደተቋረጠ የተነገረ ቢሆንም፣ በ2007 ዓ.ም. ሙሉውን ጊዜ ጭብጥ እየተያዘና ማስረጃ እየተሰማ ክርክር ሲያደርጉባቸው መክረማቸውን ለጉባዔው ያቀረቡት አቤቱታ ያስረዳል፡፡ ከዓመት በላይ ሲከራከሩባቸው የከረሙባቸው ክሶች ላይ ብይን ሳይሰጡ ማለፍ በነሱ ላይ መቀለድ መሆኑንም አክለዋል፡፡
ዳኝነት ቀላል ሥራ አለመሆኑንና በዳኝነት የሚፈጸም ስህተት ቀላል አለመሆኑን የጠቆሙት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ የተከሰሱበት መዝገብ ለአንድ ዓመት ሲቆይ በትዕግሥት የጠበቁት ዳኞቹ ፋይሉን በጥልቀት ከሕግና ከማስረጃ አንፃር እየመረመሩት እንደሆነና ሰፊ ጊዜ አስፈልጓቸው ነው በማለት የፍትሕ ሥርዓቱን ከማገዝ አንፃር ቢሆንም፣ የተሰጠው ብይን ግን ስሜታቸውን በእጅጉ የጎዳው መሆኑን ለጉባዔው ገልጸዋል፡፡  
በየቀጠሮው እየቀረቡና ማንነታቸው በዳኞቹ እየተረጋገጠ ሲከራከሩ መክረማቸውን የገለጹት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ ችሎቱ ሐምሌ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ሌላ ትዕዛዝ መስጠቱን ገልጸዋል፡፡ ተከሳሾቹ (አቤቱታ አቅራቢዎቹ) በማረሚያ ቤት መኖራቸው በዓቃቤ ሕግ በኩል እንደተነገረው ፍርድ ቤቱ ገልጾ፣ የተቋረጠው ክስ እንዲቀጥል ብሎ የሰጠው ትዕዛዝ ደግሞ ከምንም በላይ እንዳሳዘናቸውና ቀልድ እንደሆነባቸው አስረድተዋል፡፡
ዓቃቤ ሕግ በመሠረተባቸው ክስ ላይ የሰውና የሰነድ ማስረጃዎችን አሰምቶ ከጨረሰ በኋላ ለአንድ ዓመት ቆይተው የሰሙት ብይን እንዳሳዘናቸው የገለጹት ተከሳሾቹ፣ የተሰጣቸውን ብይን ሲመለከቱት የቀረበው ማስረጃ ለቀረበባቸው ክስ ያለው የይዘት፣ የአግባብነትና የብቃት ሁኔታን ሳይተነትኑ ጭብጥ ለይተው ሳይመዝኑ መሆኑን በአቤቱታቸው ገልጸዋል፡፡
ዳኞች በእያንዳንዱ መዝገብ ላይ ጉዳዩን ከሕግና ከማስረጃ አንፃር በምን ሁኔታ እንደመረመሩት፣ የቀረቡ ማስረጃዎች ለክሱ ያላቸውን አግባብነትና የማስረዳት ብቃት እንዴት እንደመዘኑት፣ የቀረቡት ማስረጃዎች ክሱን በምን መጠን እንዳስረዱት በብይናቸው ትንታኔ ላይ መግለጻቸው ጉዳዩን በተገቢው ትጋት መመርመራቸውን ለማሳየት መሠረታዊ ጉዳይ ቢሆንም፣ በእነሱ ላይ ተግባራዊ አለመሆኑ እንዳሳዘናቸው አቤቱታ አቅራቢዎቹ አስረድተዋል፡፡ የተሰጠባቸው ብይን ከቀረቡባቸው ብዛት ያላቸው ተደራራቢ ክሶች አንፃር በምን ጭብጥ መከላከል እንዳለባቸው የሚገልጽ ነገር እንደሌለም አክለዋል፡፡
የችሎቱ ዳኞች በሠሩት ብይን የፈጸሙት ስህተት ከፍተኛ ቸልተኝነት የታየበት ተግባር መሆኑን የጠቆሙት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ በአዋጅ ቁጥር 684/2002 አንቀጽ 13/2 መሠረት በገለልተኛ ባለሙያዎች ተመርምሮና በጉባዔው ታይቶ በዳኞቹ ላይ የዲሲፕሊን ቅጣት እንዲወሰንባቸው ጠይቀዋል፡፡
በተከሳሾቹ ላይ የፌዴራል ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ያቀረበባቸው ክስ እንደሚያስረዳው  የባጃጅ መገጣጠሚያ ፋብሪካ እኗቋቁማለን በማለት ወደ አገር ውስጥ ከገቡና የኢንቨስትመንት ፈቃድ ከወሰዱ በኋላ ለኢትዮጵያውያኖች ብቻ በተከለለ የሥራ ድርሻ ውስጥ በመሰማራት 871,410,695 ብር ከኢትዮጵያ ማሸሻቸውን ጠቁሞ ነበር፡፡ በሕገወጥ  ተግባር ላይ በመሰማራት መንግሥት ሊያገኝ የሚችለውን ገንዘብ (የተጠቀሰውን) ማሸሻቸውን ዓቃቤ ሕግ እንደ ክሱ ማስረዳቱን ፍርድ ቤቱ ገልጾ፣  እንዲከላከሉ ሲል ሰኔ 23 ቀን 2008 ዓ.ም. ብይን መስጠቱን መዘገባችን ይታወሳል፡፡
 Source: ethiopianreporter

No comments: