Tuesday, April 7, 2015

የምርጫ አስፈፃሚዎች የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን ውሳኔ አንቀበልም አሉ

‹‹ሰበር ሰሚ ችሎት የሚባል አናውቅም›› የምርጫ አስፈጻሚዎች
በምዕራብ ጎጃም ዞን የወንበርማ ወረዳ ምርጫ ክልል የምርጫ አስፈጻሚዎች የአማራ ብሄራዊ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት የሰጠውን ውሳኔ አንቀበልም ማለታቸውን የምዕራብ ጎጃም ዞን የሰማያዊ ፓርቲ አስተባባሪ አቶ አዲሱ ጌታነህ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡
የአማራ ብሄራዊ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት መጋቢት 18/2007 ዓ.ም በምርጫ ቦርድ ትዕዛዝ የተሰረዙት የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎች ‹‹ከምርጫ የተሰረዙት ያለ አግባብ በመሆኑ፣ መምረጥና መመረጥ ህገ መንግስታዊ መብታቸው ነው›› በሚል ወደ ዕጩነት እንዲመለሱ ውሳኔ መስጠቱ ይታወቃል፡፡
የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት እስካሁን 16 ያህል የሰማያዊ ፓርቲ ዕጩዎች ወደ ዕጩነታቸው እንዲመለሱ ቢያዝም የምርጫ አስፈጻሚዎች ‹‹ሰበር ሰሚ ችሎት የሚባል አናውቅም›› በሚል የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን ውሳኔ አንቀበልም ማለታቸውን አቶ አዲሱ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ አቶ አዲሱ አክለውም ‹‹የምርጫ አስፈጻሚዎች በብቃታቸው ሳይሆን በታማኝነታቸው ስለሚመረጡ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ለመቀበል ፈቃደኛ አልሆኑም›› ብለዋል፡፡

No comments: