Thursday, April 23, 2015

በድርድር የተሸጡ ነፍሶች?


በእያስፔድ ተስፋዬ
አይ ኤስ የተባለው ቡድን በሊቢያ ለምን ጥቃቱን በኢትዮጵያውያን ላይ ለይቶ በማነጣጠር ፈፀመ? የሚለው ለብዙዎች ጥያቄ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ከመታገታቸው በፊት ሰንደቅ ጋዜጣ የውጭ ሀገር ዜጎችን በማረድ የሚታወቀው የአይ ኤስ ኤሱ ጆን የቅርብ ጓደኛ የሖነው ኢትዮጵያዊ አዲስ አበባ ማዕከላዊ እስር ቤት ውስጥ መታሰሩን ዘግቦ ነበር፡፡ ከቀናት በኋላ ደግሞ የታሳሪው ቤተሰቦች ታሳሪው ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት እየደረሰበት ነው በሚል ቅሬታ ማሰማታቸው ተዘግቧል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ በአሰቃቂ ሁኔታ ከመታረዳቸው ቀደም ብሎ ደግሞ ኢህአዴግ ከተቃዋሚዎቹ ጋር በቴሊቪዥን በተከራከበት ወቅት የወቅቱ ተከራካሪ አቶ ሬድዋን ሁሴን የአራጁ የጆን ጓደኛ ያሉት ግለሰብ ኢትዮጵያ ውስጥ ታስሮ እንደሚገኝና በክርክሩ ወቅት አሳውቀዋል፡
የኢትዮጵያ መንግስት ዜጎቻችን በአሰቃቂ ሁኔታ ከታረዱና ከተገደሉ በኋላ የተለያዩ አገራት መንግስታት፣ ሚዲያዎች፣ ራሱ አይ ኤስ ኤስ የታረዱትን ኢትጵያውያን ናቸው ባለበት፣ እንዲሁም ለ29 ደቂቃ በቆየው ቪዲዮ ተጎጅዎቹ ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን የሚያሳይ ሆኖ እያለ የኢትዮጵያ መንግስት ‹‹ኢትዮጵያዊ መሆናቸውን ላጣራ›› በሚል ትኩረት አለመስጠቱ ይበልጡን ጥያቄ አስነስቷል፡፡ ግብጽንና ሌሎችም ዜጎቻቸው የታረዱባቸው አገራት አፀፋ እርምጃ ሲወስዱ የኢትዮጵያ መንግስት ግን ይህን ሊያስብ ቀርቶ በዜጎቻችን ላይ የተወሰደው እርምጃን የተቃወሙ ዜጎች ላይ እርምጃ በመውሰድ ላይ መሆኑ አንድ አስገዳጅ ነገር ገጥሞት እንደሆነ መገመት ይቻላል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት ከሽብር ጋር በተያያዘ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚደረጉ ዘመቻዎችን የራሱን ስብዕና ለመገንባት የሚጠቀም መሆኑና ይህንንም በሶማሊያና በሌሎች ግጭት ባለባቸው አገራት ሰራዊት ለማስገባት ችግር እንደሌለበት አሳይቷል፡፡ በቅርቡም በሳውዲ መሪነት የመን ላይ የሚደረገውን ጦርነት እንደሚደግፍ መግለጹ ይታወቃል፡፡ ይህ በሆነበትኢትዮጵያውያንን ያረደው፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ የተወገዘውና በዓለም ማህበረሰብ (መንግስታት) ዘንድ የዲፕሎማሲና የገንዘብ እገዛ የሚያስገኝነት አይ ኤስ አይ ኤስ ላይ ለመዝመትም ፍላጎት ሊኖረው እንደሚችል መገመት ቀላል ነው፡፡ ይህን ዘመቻ ኢትዮጵያ ውስጥ አለ ለሚለው ‹‹ሽብርተኝነት››እና ‹‹አክራሪነትም›› በሽፋንነት በመጠቀም ስልጣኑን ለማራዘም መልካም እድል ሊፈጥርለት ይችል ነበር፡፡
አቶ ሬድዋን ሁሴን መንግስት ባልወሰነበት ሁኔታም ይሁን ለፀረ ሽብር ዘመቻ ትኩረት እንደሰጡና ምንም አይነት አፀፋ አያመጣም በሚል በክርክሩ ወቅት ‹‹የእኛም አገር ዜግነት ያላቸው አሸባሪዎችኮ ተይዘዋል፡፡ የአራጁ ጆን ተብሎ የሚጠራው አይ ኤስ አይ ኤስ አባል የሆነው ግለሰብኮ እኛ ጋር ተይዞ ተፈርዶበታል›› ብለው ከተናገሩ ከሳምንታት በኋላ በኢትዮያውያን ላይ ይህ መንግስት አፀፋ ለመስጠት ወደኋላ የሚልበት አደጋ ደርሷል፡፡
አይ ኤስ አይ ኤስ የጃፓንና የሌሎች አገራትን ዜጎች ከያዘ በኋላ በገንዘብ መደራደሩ ይታወሳል፡፡ ከኢትዮጵያ ጋር የሚመሳሰለው ደግሞ በሊባኖስ የተፈፀመው ነው፡፡ አይ ኤስ አይ ኤስ ሁለት አባላቱን አስራ የነበረችውን ሊባኖስን ዜጎች ይዞ አባላቱን እንድትለቅለት ተደራድሮ ነበር፡፡ ሊባኖስ ፈቃደኛ ባለመሆኗ አይ ኤስ የሊባኖስን ዜጎች አርዷል፡፡ አይ ኤስ አይ ኤስ ኢትዮጵያውያንን ከማረዱና ከመግደሉ በፊት የጆን ጓደኛ ነው የተባለውን ሰው እንዲለቅ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ላለመደራደሩም እርግጠኛ መሆን አይቻልም፡፡ አይ ኤስ ኢትዮጵያውያንን ማገታቸውን ከገለፀ በኋላ በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ታጋቾቹን ለማስለቀቅ የተደረገ ወይም ሊደረግ የሚችል ነገር ነበር ወይ? እነዚህ እና እነዚህን መሰል ግልፅ ሊሆኑ የሚገባቸው ጥያቄዎች እንዳሉ ሆኖ የኢህአዴግ መንግስት በቅጡ ለህዝብ ይፋ ያላደረገው እና ከ1 ወር በፊት ያሰረው የአይ ኤስ ቡድን አባል (በአይ ኤስ ውስጥ ከፍተኛ ቦታ የነበረው ግለሰብ) ጉዳይ ከምን ደረሰ? የአሁኑ በኢትዮጵያን ላይ ያነጣጠረው የአይ ኤስ ጥቃት የኢህአዴግ መንግስት ካሰረው ከዚህ የአይ ኤስ አባል ጋር ይገናኛል ወይ?
አይ ኤስ ኢትዮጵያውያንን በሚያግትበት ወቅት ከኢትዮጵያ መንግስት የሚፈልገው ነገር አለ ወይ? አይ ኤስ 28 ኢትዮጵያውያንን አርዶ አሁን ደግሞ ሌሎችን ለማረድ አግቶ እንደሚገኝ በተለያዩ ሚዲያዎች እየተገለፀ ባለበት ወቅት የኢትዮጵያ መንግስት አስሮት የሚገኘውን የአይ ኤስ አባል ጉዳይ ምን ለማድረግ አስቧል? እነዚህ ሁሉ የተሸፋፈኑ እና የተድበሰበሱ ጉዳዮች ባሉበት ወቅት የመንግስት ኮሚኒኬሽኑ ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን በአንድ ፓርቲ ላይ ያነጣጠረ ውንጀላ እና ፍረጃ በሚዲያ እየወጣ ከሚያወራ ከህዝብ ድብቀው የያዙትን ነገር ግልፅ ቢያደርጉ እና የህዝብን ቁጣ ቢያስታግሱ ይሻላል፡፡
በቪዲዮው ላይ የምትመለከቱት በመጀመሪያው የምርጫ ክርክር ወቅት አቶ ሬድዋን ሁሴን የኢህአዴግ መንግስት በቁጥጥር ስር ስላዋለው የአይ ኤስ አባል የሚናገርበት ክፍል ነው፡

No comments: