Tuesday, April 21, 2015

(ሰበር ዜና) የሊቢያውን ግድያ በመቃወም በአ.አ. ድንገተኛ ሰላማዊ ሰልፍ እየተደረገ ነው * ወደ ቤተመንግስት ያመራው ሕዝብን ፖሊስ ቢመልሰውም መስቀል አደባባይ እየተሰበሰበ ነው

cherkos addis ababa

* ፌደራል ፖሊስ ለሐዘን የወጣውን ሕዝብ መደብደብ እና ማሰር ጀመረ
* ሐዘናቸውን የመኪና ጡሩምባ የሚያሰሙ ሹፌሮችን እያዋከበ ነው
* ሕዝቡን ከመስቀል አደባባይ ለመበተን ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሠራዊት ሰፍሯል

(ዘ-ሐበሻ) በሊቢያ አይሲኤል 28 ኢትዮጵያውያንን በአሰቃቂ ሁኔታ ከገደለ በኋላ የኢትዮጵያ ሕዝብ ቁጣውን በተለያየ መንገድ እየገለጸ ይገኛል:: በስልጣን ላይ ያለው ይህ ሁሉ ሕዝብ በአሰቃቂ ሁኔታ ሕይወቱን አጥቶ ለጉዳዩ ትኩረት አለመስጠቱ ያንገሸገሸው ሕዝብ በአዲስ አበባ በራሱ አነሳሽነት ከቤቱ ተነስቶ ወደ ቤተመንግስት ያመራ ሲሆን የመንግስት ወታደሮች እየመለሷቸው ይገኛሉ:: ሰልፈኛው “ከቤተመንግስት የምታስመልሱን ከሆነ መስቀል አደባባይ ሆነን እናለቅሳለን… መንግስት የለንም” በሚል ተቃውሞውን እያሰማ ይገኛል::
ፖሊስ ለሐዘን የወጣውን ሕዝብ ወደ ቤቱ እንዲመለስ እያሰገደደ እንደሆነ የገለጹት የዘ-ሐበሻ ምንጮች
ተከብረሽ የኖርሽ በአባቶቻችን ደም፣
እናት ኢትዮጵያ የደፈረሽ ይውደም
እያለ መዝሙር እንደሚያሰማም አስታውቀዋል:: ፌደራል ፖሊሶቹ መንግስት ሐሙስ የራሱን ሰልፍ ስለሚጠራ ወደ ቤታችሁ ተመለሱ እያሉ ቢያግባቡም “እንዴት እስከ ሐሙስ ጠብቁ ትሉናላችሁ?” የሚል ጥያቄ እያነሳም እንደሆነ ታውቕል::
‹‹መንግስት የሌለው ኢትዮጵያ ብቻ ነው!››
‹‹መንግስት የሌለን እኛ ብቻ ነን!››
እያለ መፈከር እያሰማ ወደ መስቀል አደባባይ የሚተመው ሕዝብ ቁጥር እየጨመረ ነው::
ጉዳዩን ተከታትለን እንዘግባለን::
Source: Zehabesha

No comments: