Wednesday, September 18, 2013

የሰማዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል

ሰማዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ለሰንደቅ ጋዜጣ ሰላማዊ ሰልፉን በተመለከተ እንደገለጽት፤ “ለአዲስ 

አበባ አስተዳደር የሰላማዊ ሰልፍና የህዝባዊ ስብሰባ ፈቃድ ጽ/ቤት ደብዳቤ ጽፈናል። ተጨማሪ ማብራሪያም 

አስገብተናል። በአካልም ሄደንም አነጋግረናል። ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ እንደምንችል ተግባብተናል። የተለየ ፍላጎት 

ወይም ምክንያት ቢኖራቸው በአስራ ሁለት ሰዓት ውስጥ ሊያሳውቁን እንደሚገባ ሕጉ ያዛል። የተለየ ነገር ስለመኖሩ 

ያሳወቁን ነገር የለም። ስለዚህም ሰልፉን ለማካሄድ እንችላለን። ካደረግነው ውይይት መገንዘብ እንደቻልኩት 

በመስቀል አደባባይ ላይ ሰልፉ እንዲደረግ ማቅማማት ይታይባቸዋል። ለአንድነት ፓርቲም ወደፊት የሰልፉ ቦታ 

እንደሚገለጽላቸው እንጂ የተለየ ነገር አልተገለጸላቸውም” ብለዋል።


አያይዘውም፤ “ከመንግስት የምንፈልገው የአስተዳደር ድጋፍ ብቻ ነው። ሰላማዊ ሰልፍ ለሚወጣው ሕዝብ ደህንነት 

ጥበቃ እንዲደረግልን ብቻ ነው የምናሳውቀው። ሰልፍን በተመለከተ ግን ስላሳወቅን ከአስተዳደሩ የተለየ ደብዳቤ 

አንጠብቅም” ሲሉ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ ፍቃድ እንደማይጠይቁ አስረድተዋል።


“አስተዳደሩ ሰላማዊ ሰልፉን ቢያዛውረው ከአንድነት ፓርቲ ጋር ሠልፉን ቀድሞ ማድረግ እና አለማድረግ 

ሊያስከትል የሚችለው ፖለቲካዊ ፋይዳ ይኖረው ይሆን?” ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፤ “በመጀመሪያ 

ደረጃ ሰልፉ አይሰረዝም። የመሰረዝ ፍላጎት አስተዳደሩ ቢኖረው እንኳን በዚህ በዚህ ምክንያት ሰልፍ ማድረግ 

አትችሉም ብለው ከአስራ ሁለት ሰዓታት በፊት ምላሽ መስጠት ነበረባቸው። ሰኞ ባደረግነው ውይይት ላይም አቶ 

ማርቆስም፣ አቶ አሰግድም በዚህ በኩል ያሉን ነገር የለም። ስለዚህም ለመሰረዝ የሚያስችላቸውን የሕግ 

ድጋፍ የላቸውም። በወቅቱም ደብዳቤ ጽፈው ለመስጠት ከንቲባ ድሪባ ኩማ በሀገር ውስጥ የሉም ብለውናል። 

ይመስለኛል እሳቸው ጅቡቲ ሄደዋል። ከሁለት ቀን በኋላ ይመለሳሉ ተብለናል። ሆኖም እኛ በአካል ያነጋገርናቸው 

የተለየ አመለካከት ካላቸው ከሚል መነሻ እንጂ ደብዳቤ ፈልገን አልነበረም” ሲሉ ማብራሪያ ሰጥተዋል።

አቶ ማርቆስ ብዙነህ የአ/አ ከተማ አስተዳደር የሠላማዊ ሠልፍና የህዝባዊ ስብሰባ ማሳወቂያ ፅ/ቤት ኃላፊ 

በበኩላቸው፣ “ከፓርቲው ጋር ተነጋግረናል። ከፒያሳ ወደመስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ አንድ ብቻ 

በመሆኑ ሁኔታውን ማጤን ስላለብን የምንሰጠውን ውሳኔ ክቡር ከንቲባው ሲመጡ እንደምናሳውቃቸው 

ነግረናቸዋል” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል። አያይዘውም፣ “ማሳወቅ ብቻ በቂ ነው የሚባለው ነገር ተገቢ አይመስለኝም። 

ሕጉም እንደዚህ አይልም” ብለዋል።

በአንድነትና በሰማዊ ፓርቲዎች የተጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ከሃይማኖት ጋር በተያያዘ “ከፖለቲካ” እና “ከመብት” 

ጥያቄ አንፃር የሚገለጽ በመሆኑ፣ ሰላማዊ ሰልፍ በሚወጣው ሕዝብ ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ እንዴት ያዩታል 

በሚል ለኢንጅነር ይልቃል ለቀረበላቸው ጥያቄ “በመጀመሪያ ደረጃ መብት ከፖለቲካ ጥያቄ ውስጥ ልታስወጣው 

አትችልም። የተነሳው የሃይማኖት ጥያቄ የፖለቲካ ጥያቄ ነው ስንል የጥያቄው መዳረሻው የፖለቲካ ስልጣን ጥያቄ 

ነው እያልን አይደለም። ምክንያቱም ይህ አይነት አቀራረብ እኛ ከቆምንበት ዓላማ አንፃር አብሮ የሚሄድ ባለመሆኑ 

ነው። ስለዚህም የሃይማኖት ጥያቄ የፖለቲካ ጥያቄ ነው በማለታችን ብቻ በሰልፉ ላይ የሚፈጥረው አንዳችም ተፅዕኖ 

አይኖርም” ሲሉ ምላሻቸውን ሰጥተዋል።

ምንጭ:- ሰንደቅ ጋዜጣ

No comments: