Wednesday, September 11, 2013

የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን አቃቤ ህግ ጉቦ ሲቀበል ተያዘ

የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን አቃቤ ህግ ጉቦ ሲቀበል ተያዘ

ዲስ አበባ ፣ መስከረም 1 ፣ 2006 (ኤፍ ቢ ሲ) የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን አቃቤ ህግ የነበረው ግለሰብ ጉቦ ሲቀበል እጅ ከፍንጅ መያዙን የፌደራል የሥነ ምግባር እና የፀረ ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ።
ግለሰቡ ጳጉሜን 4 ቀን 2005 ዓ.ም 30 ሺህ ብር ጉቦ ሲቀበል በኮሚሽኑ የክትትል ሠራተኞች እጅ ከፍንጅ ተይዟል።
ግለሰቡ የወንጀል ድርጊቱን ሊፈጽም የቻለው ከታክስ ክፍያ ጋር በተያያዘ ቀደም ሲል ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ምርመራውን አጠናቆ ክስ እንዲመሰረት ለአቃቤ ህጉ ካስተላለፈው የአንዲት ግለሰብ የክስ መዝገብ ጋር ተያይዞ ነው።
ግለሰቡ መሥሪያ ቤቱ ከአቃቤ ህግ እንዲከታተለው የተሰጠውን የክስ መዝገብ ከተቀበለ በኋላ ለግለሰቧ  በመደወል የክስ መዝገቡ እሱ ጋር መሆኑን በመናገር ፤ ጉዳዩን አይልሻለሁ በማለት የማይገባውን ጥቅም ለማግኘት ገንዘብ እንድትሰጠው መጠየቁን ኮሚሽኑ አመልክቷል።
በዚሁ መሠረት መጀመሪያ 5 ሺህ ብር ጉቦ ከተቀበለ በኋላ ተጨማሪ 30 ሺህ ብር እንዲሰጠው ግለሰቧን ጠይቋታል።
ይህ ጥቆማ የደረሰው ኮሚሽኑ ተገቢውን ክትትል በማድረግ አቃቤ ህጉን በዕለቱ ካዛንቺስ አካባቢ ከግለሰቧ እጅ 30 ሺህ ብር ጉቦ ሲቀበል እጅ ከፍንጅ ሊይዘው ችሏል።
ኮሚሽኑ በግለሰቡ ላይ ተጨማሪ የምርመራ ማስረጃ አሰባስቦ ፍርድ ቤት ለማቅረብ በሂደት ላይ መሆኑን ኢዜአ ዘግቧል።

No comments: