Saturday, March 14, 2015

የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች ከዋናው ክሳቸው ውጪ ለሁለተኛ ጊዜ የእስራት ቅጣት ተጣለባቸው

የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች ከዋናው ክሳቸው ውጪ ለሁለተኛ ጊዜ የእስራት ቅጣት ተጣለባቸው

አመራሮቹ ቅጣታቸውን በጭብጨባ ተቀብለዋል
የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛ ወንጀል ችሎት የሰጠውን ብይን በጭብጨባ በመቃወማቸው፣ ‹‹ፍርድ ቤትን በመድፈር ወንጀል›› በአንድ ሳምንት ውስጥ ሁለት ጊዜ የእስራት ቅጣት የተወሰነባቸው የአንድነት፣ የአረናና ሰማያዊ ፓርቲዎች አመራሮች፣ ሁለተኛውንም ቅጣት ረዘም ላሉ ሰከንዶች በማጨብጨብ ውሳኔውን ተቃወሙ፡፡

የአንድነት አመራር አቶ ዳንኤል ሽበሺና የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሺዋስ አሰፋ እያንዳንዳቸው በሰባት ወራት ቀላል እስራት ሲቀጡ፣ ‹‹አሻንጉሊት ፍርድ ቤት›› በማለት ፍርድ ቤቱን ተሳድበዋል የተባሉት የአረና ፓርቲ አመራር አቶ አብርሃ ደስታ፣ በዘጠኝ ወራት እስራት እንዲቀጡ ፍርድ ቤቱ መጋቢት 3 ቀን 2007 ዓ.ም. ውሳኔ ሰጥቷል፡፡
አመራሮቹ ከሦስት ቀናት በፊት ማለትም ሁለተኛው የእስራት ቅጣት ከተወሰነባቸው መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. በፊት ጥፋተኛ በተባሉበት ፍርድ ቤትን የመድፈር ወንጀል (የካቲት 26 ቀን 2007 ዓ.ም.) እያንዳንዳቸው በሰባት ወራት እስራት እንዲቀጡ መወሰኑ ይታወሳል፡፡ በመሆኑም በአንድ ሳምንት ውስጥ የአንድነትና የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች እያንዳንዳቸው በ14 ወራት እስራት ሲቀጡ፣ የአረና ፓርቲ አመራር አቶ አብርሃ ደስታ በድምሩ 16 ወራት ተቀጥተዋል፡፡
በሽብርተኝነት ወንጀል ክስ ተመሥርቶባቸው በማረሚያ ቤት እስር ላይ የሚገኙት እነዚሁ አመራሮች፣ ለፍርድ ቤቱ ያቀረቡት አቤቱታ በብይን ውድቅ ሲደረግባቸው ተቃውሞአቸውን በችሎቱ ውስጥ በጭብጨባ በመግለጻቸው የችሎቱን ሥራ በማወክ፣ ፍርድ ቤቱን በማንጓጠጥና ተራ ስድብ በመሳደብ፣ በአጠቃላይ ፍርድ ቤት በመድፈር ወንጀል ጥፋተኛ የተባሉ ሲሆን፣ የቅጣት ማቅለያ አስተያየትም አልሰጡም፡፡
የመጀመሪያው ቅጣት መጋቢት 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ሲጣልባቸው ከማጨብጨባቸውም በተጨማሪ፣ ፍርድ ቤቱን ‹‹አሻንጉሊት ፍርድ ቤት›› በማለት በመሳደባቸው፣ ባለተለመደ ሁኔታ የፍርድ ቤቱን አሠራር ማወካቸውን ፍርድ ቤቱ በውሳኔው አስረድቷል፡፡ ፍርድ ቤቱ አመራሮቹ ያደረጉትን ፍርድ ቤት የማወክ ተግባር ሲመረምረው ከባድ የወንጀል ድርጊት ሥር የሚወድቅ ሆኖ እንዳገኘው አስታውቋል፡፡ ነገር ግን ዓቃቤ ሕግም ባላመለከተበት ጉዳይ የቅጣት ማክበጃ አስተያየት እንደማይሰጥ በመግለጹ፣ የወንጀል ድርጊቱን ዝቅተኛ በሚል መያዙን ፍርድ ቤቱ አስረድቷል፡፡ በመሆኑም በአመራሮቹ ላይ ከላይ የተገለጸውን የእስራት ቅጣት መወሰኑን ግልጽ አድርጓል፡፡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ሲያስታውቅ ቅጣት የተጣለባቸው አመራሮቹ ረዘም ላሉ ሰከንዶች ያጨበጨቡ ቢሆንም በዝምታ አልፏቸዋል፡፡ እነሱ በተከሰሱበት የሽብርተኝነት ወንጀል ከተከሰሱት ውስጥ ሰባተኛ ተከሳሽ አቶ አብርሃም ሰለሞን ክሱ እንዲሻሻል ባቀረቡት መቃወሚያ መሠረት ዓቃቤ ሕግ ማሻሻሉ በመረጋገጡ፣ አሥሩም ተጠርጣሪዎች የእምነት ክህደት ቃላቸውን እንዲሰጡ ለመጋቢት 10 ቀን 2007 ዓ.ም. ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡  

No comments: