Tuesday, March 10, 2015

የሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ መልዕክት ለ6ኛ ጊዜ በሚዲያ እንዳይተላለፍ ተከለከለ

• ኢብኮ መልዕክቱ የተቋማትን ህልውና የሚክድ ነው በሚል መልሷል
• ‹‹ኢብኮ የኢህአዴግ ልሳን ሆኗል›› አቶ ዮናታን ተስፋዬ
የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኦብኮ) ሰማያዊ ፓርቲ የላከውን የቅስቀሳ መልዕክት ‹‹በህገ መንግስቱ የተቋቋሙ የዲሞክራሲ ተቋማትን ህልውና የሚክድና ተግባራቸውን የሚያንቋሽሽ›› ነው በሚል እንደማያስተካልፍ ትናንት የካቲት 30/2007 ዓ.ም ለፓርቲው በላከው ደብዳቤ ገልጾአል፡፡
ኢብኮ በህገ መንግስቱ የተቋቋሙ የዲሞክራሲ ተቋማትን ህልውና የሚክድና ተግባራቸውን የሚያንቋሽሹ›› ካላቸው መካከል ‹‹መከላከያ ሰራዊቱና ...ሌሎች የአገሪቱ ቁልፍ ተቋማት ከገዥው ፓርቲ ካድሬዎች ውጭ አልሆኑም››፣ ‹‹እውቀት የሌላቸው ካድሬዎች... እንዲመሩ ተደርገዋል››፣ ‹‹በገዥው ፓርቲ ካድሬዎች››፣ ‹‹ገዥው ፓርቲ ፖሊስን፣ ሚዲያውን፣ ደህንነቱን፣ ....ሰማያዊና ሌሎች ተቃዋሚዎችን ለማጥፋት ሲጠቀምባቸው ቆይቷል›› እና ‹‹የፓርቲ ጉዳይ የሚያስፈጽሙ›› የመሳሰሉትን ዓረፍተ ነገሮችና ሀረጎች እንደሆኑ በደብዳቤው ላይ ገልጾአል፡፡
በሌላ በኩል የሰማያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬ ሚዲያዎቹ የፓርቲውን መልዕክት እንዳያስተላልፉ የሚደረገው ህዝብ አማራጭ ሀሳብ እንዳያገኝ ስለሚፈለግና ኢህአዴግም ምንም አይነት ተቃውሞ እንዲቀርብበት ስለማይፈልግ ነው ሲል ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጾአል፡፡ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው አክሎም ‹‹ኢብኮ የኢህአዴግ ልሳን ሆኗል፡፡ በይፋ ኢህአዴግ እንዳይተች እየከለከለ ነው፡፡ ይህ በእርግጥ የኢህአዴግ ተግባር ነው፡፡ ኢብኮም ውስጥ ያለው ኢህአዴግ ነው፡፡›› ብሏል፡፡
ከአሁን ቀደም ኤፍ ኤም 96.3፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሬድዮ አገልግሎት፣ ፋና እና ኢብኮ የሰማያዊ ፓርቲን የቅስቀሳ መልዕክት የመለሱ ሲሆን ይህኛው የሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ መልዕክት እንዳይተላለፍ ሲከለከል ለስድስተኛ ጊዜ ነው፡

No comments: