Thursday, March 26, 2015

ሴት ጦማሪያን በተደጋጋሚ ሲያቀርቡት የነበረው አቤቱታ ውድቅ ተደረገ

318a893f13f5573daf0e70cc6261182f_L
ተጻፈ በ  ታምሩ ጽጌ
‹‹በቂ ማስረጃ አቅርበን አላቀረባችሁም መባሉ ተገቢ አይደለም›› ጠበቃ አመሐ መኰንን
በተጠረጠሩበት የሽብርተኝነት ወንጀል በሚያዝያ ወር 2006 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር ውለው ክስ የተመሠረተባቸውና ዋስትና ተከልክለው በማረሚያ ቤት የሚገኙት ሴት ጦማሪያን ማኅሌት ፋንታሁንና ኤዶም ካሳዬ፣ ከአያያዝ ጋር በተገናኘ
በማረሚያ ቤቱ ችግር እንዳለባቸው በተደጋጋሚ ያቀርቡት የነበረው አቤቱታ፣ ‹‹በማስረጃ የተደገፈ አይደለም፤›› ተብሎ መጋቢት 15 ቀን 2007 ዓ.ም. በተሰጠ ብይን ውድቅ ተደረገ፡፡
በማረሚያ ቤት የሚገኝ ማንኛውም ታራሚና ተጠርጣሪ የሚደረግለትን ወይም የተፈቀደለትን መብት እነሱ መነፈጋቸውን ክሱን እያየው ላለው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት 19ኛውን ወንጀል ችሎት አመልክተዋል፡፡ ጦማሪያኑ እንዳስረዱት፣ ከእናትና ከአባታቸው በስተቀር ሌላ ሰው እንዳይጠይቃቸው ተከልክለዋል፡፡ እነሱም ቢሆኑ የሌሎቹ ታራሚና ተጠርጣሪ ቤተሰቦች በማይመጡበት ሰዓት ቀርበው ለጥቂት ደቂቃዎች ብቻ እንዲያነጋግሯቸው መደረጉን አስረድተዋል፡፡
ሽብርተኛ መሆናቸው በፍርድ ቤት ተጣርቶና ተረጋግጦ ፍርድ ሳይሰጥባቸው እንደ አሸባሪ መቆጠራቸው፣ በሕገ መንግሥቱ የተደነገገውን ንፁኅ ሆነው የመገመት መብታቸውን የሚያሳጣ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ከሌሎች እስረኞች ጋር እንዳይቀላቀሉ መደረጋቸውንና ሌሎችንም ደርሰውብናል የሚሏቸውን ችግሮች በቃላቸውና በጽሑፍ ማቅረባቸውን ጠበቃቸው አቶ አመሐ መኰንን ገልጸዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ መጋቢት 15 ቀን 2007 ዓ.ም. በሰጠው ብይን ያቀረቡት አቤቱታ ተደጋጋሚ ቢሆንም በማስረጃ ያልተደገፈ መሆኑን ገልጾ፣ አቤቱታውን እንዳልተቀበለው በማስታወቅ የዓቃቤ ሕግ ምስክሮችን ለመስማት ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡
በተደጋጋሚ ለፍርድ ቤቱ ባቀረቡት አቤቱታ መሠረት የተለያዩ የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ኃላፊዎች እየቀረቡ ለፍርድ ቤቱ ማብራሪያ መስጠታቸውን ያስታወሱት ጠበቃ አመሐ፣ በተለይ አንድ የማረሚያ ቤቱ ኃላፊ ቀርበው በመነጋገር ችግሩን እንደሚፈቱት በመናገራቸው፣ ማረሚያ ቤት ድረስ በመሄድ አምስት ሰዓታት የፈጀ ውይይት ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡
በዋና ዋና ጉዳዮች ላይ በመስማማታቸው፣ ጦማሪያን ማኅሌት ፋንታሁንና ኤዶም ካሳዬ የፈለጉትን ያህል ጠያቂ ማስመዝገብ እንደሚችሉና በሌሎችም ችግሮች ላይ ተስማምተውም እንደነበር አክለዋል፡፡ ነገር ግን ተግባራዊ ማድረግ ባለመቻላቸው ጦማሪያኑ በድጋሚ ‹‹ችግራችን ሊሻሻል አልቻለም›› በማለት ለፍርድ ቤቱ ማመልከታቸውን አስታውሰዋል፡፡ ማስረጃ አልቀረበም በማለት የተሰጠው ብይንም ተገቢ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡

No comments: