Wednesday, July 8, 2015

በአዲስ አበባ ከፍተኛ የጸጥታ ጥበቃ እየተካሄደ ነው

ሐምሌ ፩ (አንድ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ከትናንት ጀምሮ በአዲስ አበባ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ የመከላከያ ሰራዊት አባላት የተጠናከረ ጥበቃ እያደረጉ ሲሆን፣ በርካታ ወጣቶችና የመንግስት ሰራተኞችም እየታፈሱ መሆናቸውን የደረሰን መረጃ ያመለክታል። በአዲስ አበባ የተቃዋሚ ሃይሎች ሰርገው ሳይገቡ ገብተዋል የሚል መረጃ ለደህንነት ክፍሉ እንደደረሰ የኢሳት ምንጮች ገልጸው፣ አሁኑ እንቅስቃሴም ከዚህ ጋር ሊያያዝ ይችላል ሲሉ ግምታቸውን አስፍረዋል። ለደህንነት ሲባል ኢሳት መረጃዎችን ይፋ ባያደርግም፣ በአንዳንድ መስሪያ ቤቶች ኢህአዴግ አባላት ሳይቀር ተይዘው ወደ አልታወቀ ስፍራ ተወስደዋል። ሰዎችን እያፈኑ የሚወስዱት ደግሞ በፓትሮል የሚዞሩ የፌደራል ፖሊስ አባላት ናቸው። የፖሊስ አባላቱ ማንንም ሳያናግሩ ወደ መስሪያ ቤት ዘው ብለው በመግባት የሚፈልጉትን ሰዎች እያፈኑ በመውሰድ ላይ መሆናቸውን ምንጮች ገልጸዋል። በሌላ በኩል ደግሞ ሰኞ እና ማክሰኞ በከፊል አዲሱ ገበያ ፣ ችሎትና በቀጨኔ መዲሃኔዓለም መንደሮች ውስጥ የሚገኙ ወጣቶች እና አንዳንድ በእድሜ የገፉ ሰዎች በፌደራል ፖሊሶች ክፉኛ ተደብድበው ታፍሰዋል። የፌደራል ፖሊሶች በወጣቶች ላይ ድብደባውን በጅምላ የፈጸሙት ፣ በአካባቢው አንድ የፖሊስ አባል ተደብድቧል በሚል ምክንያት ነው። ምሽት አካባቢ በአካባቢው ከፍተኛ ፍተሻ ሲካሄድ እንደነበር አይን እማኞች ገልጸዋል። በሌላ በኩል ደግሞ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሰራዊት ወደ ሰሜን እየተንቀሳቀሰ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ።

No comments: