Saturday, July 18, 2015

የእለት ተእለት ጥያቄዎቻችን

በናትናኤል ፈለቀ
“ለምን እጅግ አላስፈላጊ ዋጋ ታስከፍናለህ? አንተ ከሌሎች ኢትዬጲያውያን በምን ትለያለህ? በግል የደረሰብህ በደል የለ! አንተ በመረጥከው መንገድ ልጆችህ አለአባት ሲያድጉ ሌላው በሞቀ ጎጆ ልጆቹን ምንም እንልተፈጠረ እያሳደረ እኮ ነው! እነደው ለእኔ እካን ብለህ ባይሆን ለልጆችህ ስትል የሚሉህን ሁሉ እሺ ብለህ ከዚህ ብትወጣ ምን አለ? ልጆችንን አርፈን ብናሳድግስ “ የምትል ሚስት ስለሌለን ነው ?
“በእኔ እስር ምክንያት ባለቤቴ ልጆቼን ለማሳደግ ስራዋን አቁማ በሽታ ላይ ወደቀች፡፡ ልጆቼንም እነዳልንከባበብ ሆንኩ ፣ አግኝቻቸው ለማላውቃቸው ሰዎች ነጻነት ስል ከምንም አብልጨ የምወዳቸው ልጆቼ ጉሮሮ ላይ መቆም ምን ያህል ትክክለኛ ምርጫ ነው ?” የሚል ጭንቅላት የሚጠብጥ አጣብቂኝ ስለሌለብን ነው ?
“በዚህ እድሜዋ እናቴን መጦር ሲገባኝ ልጄ ታሰረ ብላ ጭንቀት ውስጥ እንድትገባ እና የአእምሮ እረፍት አንድታጣ ምክንያት ሆንካት ፣ አንድ ልጅ ወልደህ አይኔን በአይኔ አሳየኝ ልመናዋን እንካን ሳላሳካላት “ የሚል ቁጭት ስለሌለን ነው ?
“ልጅ ሆኜ እናቴ በማስፈልጋት ሰአት እናቴ ተገቢው ህክምና እንካን ማግኘት አንድትችል ሳላግዝ አጣሃት፡፡ አሁን ደሞ ሽማግሌ አባቴ እንክብካቤ በሚፈልግበት ጊዜ ጭራሽ እስር ቤት ገብቼ እሱን አመላልሳለሁ ፣ እድሜዬን ሙሉ ሊያስተምረኝ ጥሪቱን ማፍሰሱ ሳያንስ አሁንም እዳው ሆኛለሁ ፣ የልጅነት ሃላፌነቴን የምወጣበት ጊዜ አገኝ ይሆን?” የሚል አስጨናቂ ፍርሃት ውስጣችንን ስለማይበላው ነው ?
“የወጣትነትን እድሜሽን አታስበዬ፣ አይምሰልሽ ፣ እድሜሽ እየገፋ ሲሄድ ይቆጭሻል፡፡ ልክ አንደእኩዬችሽ ትዳር ይዘሽ ልጅ ወልደሽ የተረጋጋ ኑሮ አትኖሪም? ጊዜሽን አትቀልጂበት! የሚል መካሪ አጥተን ነው ?
“ትዳር ይዘን የተረጋጋ ቤተሰብ የምንመሰርትበት እቅድ ላይ ለምን እንቅፋት የሚሆን ስራ ተሰራለህ ? አላሳዝንህም? ምናልባት እኮ ከእስር ስትፈታ መውለድ የማልችልበት እድሜ ላይ ልሆን እችላለሁ? ደሞ ህይወቴ አንተ ታስረህ እየሄች እኮ ነው” የሚል እጮኛ ስለሌለችን ነው ?
“መንግስትን ማስገደድ የሚችል ጉልበት ያለን ስለመሰለን ነው ? ከእስር ወጥተን ራሳችንን የምናሳድርበት ሞያ ስለሌለን ነው ? ጀግና መባል ስለምንፈልግ ነው? እውቅና ዝና ፍለጋ ወይስ ልበ ደንዳናነት ነው? ምንድነው እስር ቤት ያስቀመጠን ?
ለሁሉም ጥያቄዎች መልሱ አይደለም ነው ፣ እነደማንኛውም ሰው ሁሉ ልንጦረው የምንፈልገው እናት ወይም አባት ፣ በእንክብካቤ ልናሳድጋቸው የምንፈልጋቸው ልጆች ፣ መስዋአትነት የከፈበት የፍቅር ግንኙነት ወይስ ትዳር አለን፡፡ ህይወታችንን ሁሉ እነሱን ለማስደሰት ስንደክም የማይሰለችን እና የማይበዛባቸው ሰዎች በእያንንዳችን ህይወት ውስጥ አሉ ፡፡ዝና ጀግና መባል ሁሉ ያለእነሱ ትርጉም ያጣበትና እስር ቤት ሆነን የምንወዳቸው እና የመኖራችን ትርጉም የሆኑትን ሰዎች ደስታቸውና ምኞታቸውን ነጥቀናቸዋል፡፡ የሚመኙትን እና የምንመኝላቸውን ህይወት እንዳይኖሩ እንቅፋት ሆነናል፡፡ የሚወዱትን ሰው ደስታ እንዳያገኝ እንቅፋት ከመሆን ህመም ጋር የታሰርነው በመታሰራችን የምናጣው ነገር ሳይኖር ቀርቶ አይደለም፡፡
ከላይ የተጠቀሱት በሙሉ የኢትዮጵያ የፓለቲካ እስረኞች የምር ድምጾች ናቸው ፡፡ ( ለዚህ ጽሁፍ ሲባልም የተፈበረከ ወይም የተጨመረ ነገር የለም) እነዚህ ጩኀቶች መልስ የሚያገኙት መቼ ይሆን; ይሄ ጥያቄ አንድ የወዳጄ የጦማሪ በፍቃዱ ጽሁፍን ያስታውሰኛል ፣ 80 ሚሊዬን እስክንደርስ እንታገላለን፡፡ “

Source: Zone9

No comments: