Monday, June 8, 2015

በሽብር የተከሰሱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች ላይ የአቃቤ-ህግ ምስክሮች መሰማት ተጀመረ


ሚዲያዎች የምስክሮችን ቃል መዘገብ አይችሉም ተብሏል

በሽብርተኝነት ተከሰው ጉዳያቸው እየታየ የሚገኙት የሰማያዊ፣ የአንድነትና የአረና ፓርቲዎች አመራሮች ላይ የአቃቤ ህግ ምስክሮች መሰማት ተጀመረ፡፡ በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ የተካተቱት አብርሃ ደስታ፣ የሺዋስ አሰፋ፣ ሀብታሙ አያሌው፣ ዳንኤል ሺበሽና ሌሎች ስድስት ተከሳሾች ላይ አቃቤ ህግ አሉኝ ያላቸውን የሰው ማስረጃዎች ምስክርነት ዛሬ ሰኔ 01/07 ዓ.ም በከፍተኛው ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ማሰማት ጀምሯል፡፡
ምስክሮች መሰማት ከመጀመራቸው በፊት አከራካሪው ጉዳይ ምስክሮቹ በግልጽ ችሎት ይሰሙ ወይስ በዝግ ችሎት የሚለው ነበር፡፡ በዚህም አቃቤ ህግ የጸረ ሽብር አዋጁ አንቀጽ 32 ላይ የተመለከተውን የምስክሮች ጥበቃ ድንጋጌ በመጥቀስና ምስክሮቹ ዛቻና ማስፈራሪያ እንደደረሰባቸው በማውሳት ችሎቱ ምስክሮችን በዝግ እንዲሰማ ጠይቋል፡፡ ተከሳሾች በበኩላቸው ህገ መንግስቱን በመጥቀስ አቃቤ ህግ ያቀረበው ምክንያት በማስረጃ ያልተደገፈ ስለሆነ ችሎቱ ግልጽ እንዲሆን ተከራክረዋል፡፡
ሶስተኛ ተከሳሺ አቶ ዳንኤል ሽበሺ ‹‹አቃቤ ህግ እስከ ሞት በሚያደርስ ወንጀል ከሶናል፤ ይህን ጉዳይ በግልጽ መከታተል አለብን፡፡ እናንተ ብቻ ሳትሆኑ የኢትዮጵያ ህዝብም መፍረድ አለበት›› በማለት ችሎቱ ምስክሮችን በግልጽ እንዲሰማ አሳስቧል፡፡ አቶ ሀብታሙ አያሌው በበኩሉ ‹‹እኛ ዋስትና ተከልክለን በእስር ቤት ነን፤ የምስክሮች ስም ዝርዝር እንኳ አልተገለጸልንም፡፡ ታዲያ ማን ነው ምስክሮች ላይ ዛቻና ማስፈራሪያ የሚያደርስባቸው?›› ሲል አቃቤ ህግ ያቀረበው ምክንያት ተቀባይነት እንደሌለው በማስረዳት ችሎቱ ግልጽ እንዲሆን ጠይቋል፡፡
አቶ ሀብታሙ ሁሉንም ተከሳሾች በመወከል እንዳስረዳው ደግሞ ፍርድ ቤቱ ምስክሮችን በዝግ የሚሰማ ከሆነ ሁሉም የግፍ ፍርደኛ ሆነው ወደ እስር ቤት ለመመለስ ዝግጁ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ ‹‹ሁሉንም ወክየ ነው የምናገረው…በዝግ ችሎት ምስክሮችን የምትሰሙ ከሆነ ዛሬውኑ የግፍ ፍርደኞች ሆነን ወደ እስር ቤት ለመመለስ ዝግጁዎች ነን፤ ከዚህ በኋላም አንዳችንም ክርክር አናደርግም፡፡››
ፍርድ ቤቱ በአቃቤ ህግና በተከሳሾች መካከል የተነሳውን ክርክር መርምሮ ብይን የሰጠ ሲሆን በብይኑ መሰረትም የአቃቤ ህግ ምስክሮች በግልጽ ችሎት እንዲሰሙ ወስኗል፡፡ ሆኖም ግን ፍርድ ቤቱ የህትመትም ሆነ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች የምስክሮችን ቃል ዝርዝር በተመለከተ መዘገብ እንደማይችሉ በብይኑ ላይ አመልክቷል፡፡
ዛሬ መሰማት የጀመረው የአቃቤ ህግ ምስክሮች እስከ ሰኔ 3/2007 ዓ.ም እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡
በዚሁ መዝገብ ተከሳሾች መካከል አምስተኛ ተከሳሽ የሆነው የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አቶ የሺዋስ አሰፋ ዳኞቹ ሲሰየሙና ስሙ ሲጠራ ከመቀመጫው ባለመነሳት በችሎቱ ላይ ተቃውሞውን ገልጹዋል፡፡ አቶ የሺዋስ ዳኞቹ ለምን እንደማይነሳ ሲጠይቁት በዝምታ ያለፋቸው ሲሆን፣ ተነስ ሲባልም ያለምንም ንግግር በተቀመጠበት ረግቷል፡፡

No comments: