Thursday, June 18, 2015

‹‹የታሰርኩት ባልሰራሁት ወንጀል ነው›› አቶ ማሙሸት አማረ



መጀመሪያ የቀረበብኝ ክስ አይ ኤስ አይ ኤስን ለመቃወም የተጠራው ሰልፍ ላይ ወጣቶችን አደራጅተህ ሁከትና ብጥብጥ ፈጥረሃል የሚል ነው፡፡ በዚህ ክስ ፖሊስ ሁነኛ ማስረጃ አለኝ ብሎ ፍርድ ቤት ቀርቦ ተከራክሯል፡፡ መንግስት በጠራው ሰልፍ ላይ ሁከትና ብጥብጥ ለማስነሳት ስለጣረ ምርጫ ላይም ተመሳሳይ ችግር ይፈጥርብናል ብሎ ማክበጃ ሁሉ አቅርቧል፡፡ ነገር ግን የሰልፉ ቀን እኔ ከምርጫ ቦርድ ጋር ባለን ክስ ፍርድ ቤት ክርክር ነበረኝ፡፡ መጀመሪያ ሰልፉ ላይ እንዳልነበርኩ ብከራከርም ሰልፉ ላይ መገኘቴን ገልጾ ሲከራከር የነበረው ፖሊስ ፍርድ ቤቱ ሚያዝያ 14/08/07 ተያዝኩ በተባለበት ሰዓት ፍርድ ቤት ውስጥ እንደነበርኩ ጻፈልኝ፡፡ ያንን ሳቀርብ ጠንካራ ማስረጃ አለ ብሎ ሲከራከር የነበረውና ሰልፉ ላይ ብጥብጥ ፈጥሯል ብሎ ያስመሰከረብኝ ፖሊስ ክሱን አንስቻለሁ አለ፡፡
ፖሊስ ክሱን በማንሳቱም በነፃ እንድለቀቅ ተደረገ፡፡ ቤተሰቦቼ የመፍቻ ወረቀት ይዘው ወደ ፖሊስ ጣቢያው ሲሄዱ ፖሊሶቹም ታስሬ የነበርኩበት ቦሌ ክፍለ ከተማ አምቼ ፖሊስ ጣቢያ ወስደው እንደሚፈቱኝ ገልጸውልኝ ከፍርድ ቤት ወጣን፡፡ ሆኖም ግን ወደ አምቼ ወስደንህ ትፈታለህ ያሉኝ ፖሊሶች በቀጥታ ወደ አዲስ አበባ ፖሊስ ጣቢያ (ሶስተኛ) ይዘውኝ መጡ፡፡
የመጀመሪያውና ፍርድ ቤት ሰልፉ ላይ እንዳልበርኩ የመሰከረልኝ ክስ አላስኬድ ሲል በነገታው ሌላ ክስ መሰረቱብኝ፡፡ በ14/08/07 እንዳልነበርኩ የሚያሳይ ጠንካራ መረጃ ሲገኝ ክሱን ከዛ በፊት አደረጉት፡፡ በመሆኑም ወደኋላ ተመልሰው በ12/08/07 እና በ13/08/07 ወጣቱን አደራጅቶ ወደ ለቅሶ ቤት በመውሰድ ብጥብጥ ፈጥሯል ብለው ከሰሱኝ፡፡ ዛሬ በነበረኝ ችሎት ዳኛዋ 5 ሺህ ብር አስይዜ ከእስር እንድለቀቅ ፈርደው ነበር፡፡ ጓደኞቼና ቤተሰቦቹ መፍቻ ይዘው ሲመጡ ግን አለቆቹ ቢሯቸውን ዘግተው ወጥተዋል፡፡ እኔን በቀላሉ መፍታት የፈለጉ አይመስለኝም፡፡
የመጀመሪያውን ክስ ፍርድ ቤት በፃፈው ደብዳቤ ውድቅ ሆኗል፡፡ አሁን ደግሞ ዳኛዋ እንድለቀቅ ወስነዋል፡፡ ሆኖም ግን ፖሊስ እኔን መፍታት አልፈለገም፡፡ አሁንም ድረስ ታስሬ የምገኘው ባልዋልኩበት ነው፡፡ የታሰርኩት ባልሰራሁት ወንጀል ነው፡፡ እንግዲህ ቀጥሎ የሚመጣውን የምናየው ይሆናል፡፡ ምን እንደሚያደርጉ አላውቅም፡፡
(ይህ ፅሁፍ ትናንት ሰኔ 9/2007 ዓ.ም የነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር ከአቶ ከማሙሸት አማረ ጋር ካደረገው ንግግር የተወሰደ ሲሆን በዛሬው ዕለት ይግባኝ እንደተጠየቀበት ለማወቅ ተችሏል፡፡)

No comments: