Thursday, February 4, 2016

የመለስ “ሌጋሲ” – የድርብ አኻዝ ዕድገት ውጤት

አንድ ውሃ እና ሁለት ለስላሳ ብር 139.97 (ግሳንግሱን ጨምሮ)
receipt

ሥልጣን የያዙ ሰሞን ሞት የቀደማቸው መለስ ሲጠየቁ የኢትዮጵያን ሕዝብ በቀን ሦስት ጊዜ እመግባለሁ ወይም ሲመገብ አያለሁ የሚል የውሸት ተስፋ ሰጥተው ነበር፡፡ “የቀማኛ ኢኮኖሚ አቀንቃኝ” የነበሩት መለስ ለሥልጣናቸው ማራዘሚያ ጥቂቶችን በሃብት እንዲወጠሩ ሲያደርጉ የተቀረውን ኢትዮጵያዊ በቀን ሶስቴ ቀርቶ በሶስት ቀን አንዴ የማይመገብ አድርገውት ተሰናብተዋል፡፡
“ሌጋሲያቸውን እንጠብቃለን፤ እናስጠብቃለን” የሚሉት ያሁኖቹ ዘራፊዎችና ተላላኪዎች አገር በሁለት አኃዝ አድጋለች፤ ኢኮኖሚው ዓለምን እያስደነቀ ነው፤ ህዳሴ ነው፤ ውዳሴ ነው፤ … በማለት በቁማቸው ይዋሻሉ፤ የጥቅም ተካፋዮቻቸውም ይህንኑ ይዘው በየቀኑ ሲያናፉ ይውላሉ፡፡
ህወሃት ስለዘረጋው የዘራፊ፤ የቀማኛ፤ የሌባ፤ ኢኮኖሚ ብዙ ሊባልበት ይቻላል፡፡ ሌብነቱን ደግሞ መለስ ራሳቸው መስክረው ነው የሞቱት፡፡ “ያስቸገረን የመንግሥት ሌባ ነው” ብለው ነበር እንደ ቆርኪ ክዳን ድንገተኛው ሞት አስፈንጥሮ ሳይወስዳቸው በፊት፡፡ የመንግሥት ሌባ ማለት የህወሃት/ኢህአዴግ ሌባ ማለት እንደሆነ ለተናጋሪውም ሆነ ለሰሚው የተሰወረ አይደለም፡፡
በፎቶው ላይ የሚታየውን ደረሰኝ ያገኘነው ከዝዋይ ቃሊቲ ቂሊንጦ ፌስቡክ ገጽ ላይ ነው፡፡ እንዲህ የሚል መረጃ አብሮ ተጽፎ ነው ፎቶው የተለጠፈው፡-receipt
“ምን አልባት ሰይጣን አሳስትዎት ወደ ማፊ ሞል ጎራ ቢሉ ግር እንዳይልዎ … ቦሌ መድሀኒአለም ፊት ለፊት የሚገኘው ማፊ ህንፃ አንደኛ ፎቅ ላይ የሚገኘው ባር በረንዳው ላይ አረፍ ብለው ሁለት ለስላሳና ግማሽ ሊትር ውሀ ቢጠቀሙ ይህ በፎቶው የሚመለከቱት ቢል ይቀርብሎታል።”
ህወሃት የመሠረተው “የኢኮኖሚ ብልጽግና” ከምዕራባውያኑ ጋር ሲነጻጸር በከሰል ጆኒያ ውስጥ እንዳለ ጥቁር አዝሙድ የሚቆጠር ሆኖ ሳለ በምዕራቡ ዓለም እንኳን የማይከፈል የዋጋ ተመን የትግራይ ነጻ አውጪ ግምባር (ህወሃት) በግፍ በሚገዛት ኢትዮጵያ ላይ ጭኖ “ገበያ መር ኢኮኖሚ ነው፤ ነጻ ውድድር ነው፤…” ይላል፡፡ ዘራፊ ሁልጊዜ ሁሉንም እየዘረፈ፤ ተዘራፊም ሁልጊዜ በዘራፊ እየተዘረፈ አይኖርም፡፡ እጅግ ግዙፍ ሸክሞችን ስትሸከም የኖረችውን ግመል ጀርባ የሚሰብረው የመጨረሻው ገለባ ነው እንደሚባለው ነው፡፡ (ጎልጉል፤ የድረገጽ ጋዜጣ)
Source: ጎልጉል

No comments: