Thursday, February 25, 2016

ዴቪድ ካሜሩን ወደ አዲስ አበባ ሊጓዙ ነው፣ አንዳርጋቸው ጽጌ እንዲፈቱ ግፊት ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የብሪታኒያው ጠቅላይ ሚኒስቴር ዴቪድ ካሜሩን በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ ለመምከር በቅርቡ ወደ ኢትዮጵያ እንደሚጓዙ የሃገሪቱ ባለስልጣናት ረቡዕ ይፋ አድርጉ።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝትም ከሳምንት በፊት ዴቪድ ካሜሩን አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንዲፈቱ ግፊትን እንዲያደርጉ የቀረበላቸውን 130 በላይ ፊርትማዎች ተከትሎ እንደሆነ ታውቋል።
የብሪታኒያ የኢሚግሬሽንና ዜጎች እንዲሁም ተጓዳኝ ጉዳዮችን የሚከታተለው ሆም ኦፊስ ምክትል ቋሚ ፅሃፊ የሆኑት ኦሊቨር ሮቢንስ ከኢትዮጵያ ባለስልጣናት ጋር በአዲስ አበባ እየመከሩ መሆናቸውን ከሃገር ቤት የተገኘ መረጃ አመልክቷል።
በጉብኝነት ላይ የሚገኙት ሃላፊው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዲቪድ ካሜሩን በቅርቡ ወደአዲስ አበባ በመጓዝ ከሃገሪቱ ባለስልጣናት ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ እንደሚፈራረም ይፋ አድርገዋል። ይሁንና፣ ሃላፊው ኦሊቨር ሮቢንስ ዴቪድ ካሜሩን መቼ ወደ አዲስ አበባ እንደሚጓዙ ዝርዝር መረጃን ከመስጠት የተቆጠቡ ሲሆን የአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጉዳይ ዋነኛ አጀንዳ እንደሚሆን ይጠበቃል።
በቅርቡ የብሪታኒያ ታዋቂ ግለሰቦችና የፓርላማ አባላት ያካተተ 135 ሰዎች ፊርማ ለዴቪድ ካሜሩን የቀረበ ሲሆን ፊርማቸውን ያሰባሰቡ አካላትም ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ እንዳርጋቸው ፅጌ የሚፈቱበትን ሁኔታ እንዲያመቻቹና ግፊትን እንዲያደርጉ አሳስበዋል። የቀረበላቸውን ፊርማ ተከትሎ ወደ ኢትዮጵያ በቅርቡ የሚጓዙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን ይህንኑ ጉዳይ ዋነኛ መነጋገሪያ እንደሚያደርጉት ተነግሯል።
የሃገሪቱ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችና ግለሰቦች የብሪታኒያ ባለስልጣናት አቶ አንዳርጋቸውን ከእስር ለማስፈታት ለዘብተኛ ሆነዋል በማለት ተደጋጋሚ ተቃውሞን ሲያቀርቡ መቆየታቸው ይታወሳል። የብሪታኒያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ የአቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጉዳይ ችላ አለመባሉን በመግለፅ አሁንም ድረስ የሁለት ሃገራት መነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖ እንደሚገኝ በቅርቡ አስታውቋል።
ከሶስት ወር በኋላ በቁጥጥር ስር ከዋሉ ሁለት አመት በሚሞላቸው አቶ እንዳርጋቸው ፅጌ የታሰሩበት ቦታ የማይታወቅ ሲሆን በቤተሰቦቻቸውን በህግ ባለሙያዎች እንድይጎቨኙ ተደርጎ ይገኛል።
ኢሳት (የካቲት 16 2008)


No comments: