Friday, February 19, 2016

በምስራቅ ሃረርጌና ወለጋ አካባቢዎች ተቃውሞ ዳግም ማገርሸቱ ተነገረ

ኢሳት (የካቲት 11 2008)
የኦሮሚያ ክልል ተቃውሞ ከሁለት ወር በፊት ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጋር በተገናኘ በተለያዩ የክልሉ ከተሞች የተቀሰቀሰው ተቃውሞ ሰሞኑን በምስራቅ ሃረርጌና ወለጋ አካባቢዎች ዳግም ማገርሸቱ ተገልጿል።
የጸጥታ ሃይሎች ተቃውሞን ለመበተን በወሰዱት እርምጃ በርካታ ሰዎች ጉዳት እንደረደረሰባቸው ለእስር እንደተዳረጉም ከሃገር ቤት የተገኘ መረጃ መልክቷል።
የፌዴራልና የክልሉ ባለስልጣናት ሶስተኛ ወሩን ያስቆጠረው ተቃውሞ በቁጥጥር ስር ውሏል ቢሉም ይኸው ተቃውሞ ዳግም ማገርሸቱን የተለያዩ አካላት በመግለጽ ላይ ናቸው። 
በምዕራብ ሸዋ በሚገኙ የገጠር መንደሮች ጭምር ቀጥሎ ባለው ተቃውሞ ቁጥሩ በአግባቡ ሊታወቅ ያልቻለ ነዋሪ መገደሉንና ለእስር መዳረጉንም ለመረዳት ተችሏል።
ሂውማን ራይትስ ዎችን ጨምሮ የተለያዩ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶችና ግለሰቦች በኦሮሚያ ክልል እየተካሄደ ባለው ተቃውሞ 150 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ይገልጻሉ። 
ይሁንና የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች እየወሰዱ ያለው እርምጃ ተጠናክሮ በመቀጠሉና በሃገሪቱ የነጻ መገናኛ ብዙሃን በአፈና ውስጥ በመሆኑ የሟቾችን ቁጥር በአግባቡ ማወቅ እንዳልተቻለ ተቋማቱ አስታወቀ።
የአውሮፓ ህብረትን ጨምሮ አሜሪካና ሌሎች አለም አቀፍ ተቋማት እየተካሄደ ያለውን የጸጥታ ሃይሎች ድርጊት በማወገዝ ድርጊቱ በገለልተኛ አካል ማጣራት እንዲካሄድበት በማሳሰብ ላይ ናቸው።
ከዚሁ ተቃውሞ ጋር በተገናኘ ለእስር የተዳረጉ የፓርቲ አባላትና ደጋፊዎችም በአስቸኳይ እንዲፈቱ እነዚሁ አካላት አሳስበዋል።


No comments: