Tuesday, April 26, 2016

መቻቻል ወይስ መቻል !!!

በአገራችን ያለው የፖለቲካ አለመግባባት እንዲፈታ በተደጋጋሚ ጥያቄ ሲቀርብ እንሰማለን፡፡ በተለይ ተቃዋሚዎች ድምጻቸውን ከፍ አድርገው በየመድረኩ ጮኸዋል፡፡ የአገራችን ጉዳይ ያገባናል ያሉ ኢትዮጵያዊያን በተመሳሳይ ሁኔታ የእርቅ ጥሪውን ድጋፍ ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ በወያኔ/ኢህአዴግ በኩል ግን ማን ከማን ተጣላና ነው እርቅ የሚያስፈልገው? ሲባል ሰምተናል፡፡ ስለ ዛሬው ከመነጋገር ይልቅ ወደ ኋላ እየተመለሱ ያለፉትን ሥርአቶች ማውገዝ እንደ ባህል ተደርጎ ቆይቷል፡፡ ይህ ደግሞ ለማንም አይጠቅምም፡፡ የአገሪቱ ጉዳይ የዜጎቿ ጉዳይ ነው ተብሎ ይታመናል፡፡ማንም ስለማንም አውቅልሃለሁ የሚልበት ጊዜ ማክተም ያለበት አሁን ይመስለኛል።
ዛሬ ወደድንም ጠላንም የመቻቻልን መርህ አምነን መቀበል የግድ ነው፡፡ የፌዝ መቻቻል ሳይሆን የእውነት መቻቻ ማለት ነው፡፡ መቻቻልን ዛሬም ቻል በሚል መርህ ለማስኬድ ከተፈለገ የትም አያደርስም፡፡ በአገሪቱ ውስጥ ልዩነትን በማጥበብ አገራዊ መግባባትን ለመፍጠር ከተፈለገ ተቀምጦ መወያየትን ይጠይቃል፡፡ ጎጂና ተጎጂ ተቀምጦ በልዩነት ላይ ለማውራት ጎጂው ቢያንስ አንድ እርምጃ ወደ ኋላ መመለስ የግድ ነው፡፡
ጎጂ አንድ እርምጃ ወደኋላ መመለስ አለበት ሲባል የገፈፈውን መብትንና ነጻነትን ማክበር፣የታሰሩ የፖለቲካ እስረኞችን መፍታት፣በህግ ሽፋን የሚፈፀም የእስራት ተግባራትን ማቆም የግድ ነው፡፡ማን አለብኝነትና ራስን ከተጠያቂነት ውጭ አድርጎ ማሰብን ማቆም ያስፈልገናል፡፡ 
ብሔራዊ መግባባትን ለማምጣት እርቅን መቀበል ተፈጥሯዊ ህግን የመቀበል ግዴታ ነው፡፡ ሰው ከሰው ጋር ብቻ ሳይሆን ሰው ከተፈጥሮ ጋር ተግባብቶ ለመኖር ሰጥቶ የመቀበል መርህን ያከብራል፡፡ ጉልበቱን ጊዜውን ሰጥቶ ላቡን በማፍሰስ መሬቱን ካረሰ በኋላ አንድ ቁና ዘር ቢዘራ ከሶስትና ከአራት ወር በኋላ ቢያንስ አንድ ኩንታል ምርት ያገኛል፡፡ ጉልበቱን ጊዜውን እውቀቱን ሸጦ ገንዘብ ያገኛል፡፡ ለብሔራዊ መግባባትም እንዲሁ ሰጥቶ መቀበል መርህን አምኖ መቀበል ተገቢ ነው፡፡ በሰጥቶ መቀበል መንፈስ የያዙትንና የሚያምኑበትን ሀሳብ የተወሰነውን በመልቀቅ የተቃራኒውን አካል ሀሳብ መቀበል የግድ ነው፡፡ ‹‹የእኔን አለቅም የአንተንም አልቀበልም›› ብሎ ብሔራዊ መግባባት መፍጠር አይቻልም፡፡ የእኔ እምነትና አስተሳሰብ እንከንየለሽ፣ የሌላው ደግሞ ሙሉ በሙሉ ስህተት ነው ብሎ ማመን አይቻልም፡፡ እዚያም ቤት እውነት አለ ብሎ ማመን ግድ ነው፡፡
ዛሬ የሚያስፈልገን መቻቻል እንጂ መቻል አይደለም፡፡ የመሳሪያ እና የፕሮፓጋንዳ አገዛዝ እስከተወሰነ ጊዜ ሊያኖር ይችላል፡፡ ዘላለማዊ ግን ሊሆን አይችልም፡፡ ራስን እንደ ንጹህ ሌላውን ደግሞ እንደ ፍጹም ወንጀለኛ በመቁጠር ብሔራዊ መግባባት ማምጣት አይቻልም፡፡ ራስን ለብሔራዊ መግባባትና ለብሔራዊ እርቅ ማዘጋጀት የበታችነት ወይም የሽንፈት ምልክት ሳይሆን የጀግንነት ተግባር ነው፡፡ የሰለጠነና ዘመናዊ የችግር መፍቻ ዘዴ ነው፡፡ ከአንገት ሳይሆን ከአንጀት እርቅ ያስፈልገናል፡፡ጊዜውም አሁን ነው፡፡ በአገራችን ለተፈጠረው አለመግባባት ተጠያቄ ሌላውን አካል አድርጎ በሌላው ላይ ጣት ከመቀሰር ወይም አለመግባባት አልተፈጠረም እያሉ በራስ ላይ ከማላገጥ ይልቅ እያንዳንዱ ጣቱን ወደ ራሱ እያሳየ በቅንነት አገራችንና ህዝቡን እንታደገው፡፡ ለአገራችን ሕዝብ ማን አለው ? አይ ባይ ያጣን አንሁን !! ሕዝባችንን እንውደድ !!
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!

No comments: