Sunday, April 24, 2016

በጋምቤላ ክልል በድጋሚ በ21 ዜጎች ላይ ግድያ ተፈጸመ


Gambela

መንግሥት የታገቱት ሕፃናት ያሉበትን ቦታ አውቄያለሁ አለ
ባለፈው ሳምንት ዓርብ ለቅዳሜ አጥቢያ በጋምቤላ ክልል የደረሰው አሰቃቂ ጭፍጨፋ የፈጠረው ሐዘን ሳይሽር፣ በድጋሚ ሌላ አሰቃቂ ግድያ በ21 ዜጎች ላይ ተፈጸመ፡፡
ሐሙስ ሚያዝያ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ረፋድ ላይ በጋምቤላ ክልል ጀዊ ስደተኞች ካምፕ የሚኖሩ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች፣ 21 ሰዎች ገድለው ሰባት ሰዎች ማቁሰላቸውን ሪፖርተር ከሥፍራው የደረሰው መረጃ አመልክቷል፡፡
የግድያው ምክንያት ሐሙስ ረፋድ ላይ በጋምቤላ ከተማ ከሚገኙ ስድስት ካምፖች አንዱ በሆነው ጀዊ ስደተኞች ካምፕ ውኃ የሚያመላልስ ቦቴ ተሽከርካሪ፣ ብስክሌት ይጫወቱ የነበሩ ሁለት ሕፃናት ስደተኞች ላይ አደጋ ማድረሱ ነው፡፡ በድንገተኛው የተሽከርካሪ አደጋ የሕፃናቱ ሕይወት ያለፈ ሲሆን፣ ስደተኞቹ ይህ አደጋ ሆን ተብሎ የደረሰ ነው በማለት ወዲያውኑ በኢትዮጵያውያን ላይ አደጋ ማድረስ ጀመሩ፡፡
በአደጋው እስካለፈው ዓርብ ድረስ የ21 ሰዎች አስከሬን ተሰብስቦ ወደ ጋምቤላ ሆስፒታል የተጓጓዘ ሲሆን፣ የሟቾች ቁጥር ከዚህ በላይ ሊሆን እንደሚችል የጋምቤላ ነዋሪዎች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ስደተኞቹ ደቡብ ሱዳናውያን ድንጋይ፣ ገጀራና ጦር በመጠቀም በሥፍራው በአሸዋ ማውጣት ሥራ ላይ የተሰማሩ ዜጎች ላይ ጭፍጨፋ መፈጸማቸው ተነግሯል፡፡ ጭፍጨፋው የተካሄደበት ቦታ ጫካማ በመሆኑ ራሳቸውን ለማዳን ወደ ጫካ የሸሹ ሰዎች በመኖራቸው፣ በወቅቱም ያልተገኙ ሰዎች ስለነበሩ የሟቾች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ምንጮች ተናግረዋል፡፡
የቆሰሉ ሰዎች ጋምቤላ ክልል ውስጥ በምትገኘው ቦንጋ ከተማ ሕክምና እየተደረገላቸው መሆኑ ተገልጿል፡፡ ይህ ጭፍጨፋ የተሽከርካሪ አደጋን ምክንያት ያድርግ እንጂ፣ የክልሉ ነዋሪዎች መሰንበቻውን በክልሉ የተከሰቱት ጭፍጨፋዎች ከዚህ ቀደም ታይተው በማይታወቁ መንገዶች የተፈጸሙ በመሆናቸው ከፍተኛ ሥጋት እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል፡፡
ጋምቤላ ሚያዝያ 7 ቀን 2008 ዓ.ም. ዓርብ ለቅዳሜ አጥቢያ ከንጋቱ 11፡00 ሰዓት በደረሰው ጭፍጨፋ የ182 ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ፣ ከዚህ ቀደም ባሉት ቀናት ከነበረው ግድያ ጋር በድምሩ የ208 ሰዎች ሕይወት ማለፉ ታውቋል፡፡ 72 ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸው ይታወቃል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ 36 ሕፃናት በዕለቱ ታፍነው ሲወሰዱ ቀደም ባሉት ቀናት ከተወሰዱት ጋር የታፈኑት ሕፃናት ቁጥር 108 ደርሷል፡፡ ከ2,000 በላይ ከብቶች ተነድተዋል፡፡ ይህ ዘግናኝ ክስተት መላ ኢትዮጵያውያን ለከፍተኛ ሐዘን ዳርጎ ባለበት ወቅት፣ በድጋሚ በሳምንቱ ተመሳሳይ ጭፍጨፋ መከሰቱ ብዙዎችን አስቆጥቷል፡፡
ለሚያዝያ 7 ቀን ጥቃት መንግሥት አፀፋዊ ዕርምጃ በመውሰድና ሕፃናቱን ለማስለቀቅ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ አቶ ተወልደ ሙሉጌታ ዓርብ ሚያዝያ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. ለጋዜጠኞች እንደገለጹት፣ ታፍነው የተወሰዱ ሕፃናት ያሉበት ቦታ ተለይቷል፡፡ አቶ ተወልደ ከዚህ በተጨማሪ በኢትዮጵያ ላይ የደረሰው ጥቃት ከጀርባው የፖለቲካ አጀንዳ መኖር አለመኖሩ፣ ጥቃቱን ያደረሰው አካል ማንነት እየተመረመረ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የጋምቤላ ክልላዊ መንግሥት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጋትሉዋክ ቱት ይህንን ግድያ በተመለከተ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፣ ሕዝቡን ለማረጋጋት በተለያዩ ቦታዎች በመንቀሳቀስ ላይ እንዳሉ ገልጸው፣ በሁለተኛው ግድያ ዙሪያ ሙሉ የተሟላ መረጃ እንደሌላቸውም ጠቁመዋል፡፡ ነገር ግን ችግሩ የተከሰተው በተሽከርካሪ አደጋ ምክንያት ለበቀል በተነሱ ስደተኞች መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡
ኢትዮጵያ 272,648,300 የተለያዩ አገሮች ስደተኞችን ታስተናግዳለች፡፡ ከዚህ ውስጥ በጋምቤላ ክልል የሚገኘውና ይህ ጭፍጨፋ የተፈጸመበት ጀዊ ስደተኞች ካምፕ ውስጥ 48,648 ስደተኞች ይገኛሉ፡፡ ስደተኞችን የሚያስተዳድረው የኢትዮጵያ ስደተኞችና ስደት ተመላሾች ባለሥልጣን በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጥ በሪፖርተር የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡
ምንጭ – ሪፖርተር

No comments: