Tuesday, May 13, 2014

በዝዋይ የርሃብ አድማ የመቱ እስረኞች ተደበደቡ

በዝዋይ የርሃብ አድማ የመቱ እስረኞች ተደበደቡ


ቤተሰቦቻቸው እንድናያቸው አልተፈቀደልንም ብለዋል

በዝዋይ ወህኒ ቤት የሚገኙት ፖለቲከኞች አቶ ዘሪሁን /እግዚአብሄር፣ናትናኤል መኮንን፣ክንፈሚካኤል ደበበና አንዷለም አያሌው የርሃብ አድማ ለሁለት ሳምንታት ያህል ማድረጋቸውን ተከትሎ ድብደባ ተፈጽሞባቸው በኮንቴነር ውስጥ ታስረው እንደሚገኙ የእስረኞቹ ቤተሰቦች አስታወቁ፡፡
በድብደባው ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው የተነገረባቸው የኢትዮጵያ ብሄራዊ አንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር የሆኑት አቶ ዘሪሁን በማረሚያ ቤቱ የህክምና መስጫ እርዳታ እየተደረገላቸው እንደሚገኝም ባለቤታቸውና ልጃቸው በእንባ ተውጠው አስታውቀዋል፡፡ የአቶ ዘሪሁን ባለቤት ወይዘሮ ፎዚያና ልጃቸው ሊዲያ ዘሪሁን ለጥየቃ ወደ ዝዋይ ባመሩበት ወቅት ጥበቃ ላይ የነበሩ ፖሊሶች ወደ ውስጥ እንዲገቡ ሳይፈቅዱላቸው እንደቀሩ በመግለጽ‹‹ለምን እንደማያገናኙኝ ስንጠይቃቸው ለቀጣዩቹ አራት ወራቶች እንደማናገኛቸው ነግረውናል›› ብለዋል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ የአንድነት ፓርቲ የብሄራዊ ምክር ቤት አባል የሆነው የአቶ ናትናኤል ባለቤት ወይዘሮ ፍቅርተ ዝዋይ ቢሄዱም ናትናኤልን ለማግኘት ሳይታደሉ ተመልሰዋል፡፡
የእስረኞቹ ቤተሰቦች ከውስጥ አገኘነው እንደሚሉት መረጃ ከሆነ የርሃብ አድማውን እንዲያቆሙ ድብደባ የተፈጸመባቸው በመሆኑ ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲገናኙ አልተፈቀደላቸውም፡፡ ታሳሪዎቹ ከድብደባው በኋላ ከየክፍሎቻቸው እንዲወጡ ተደርገው በኮንቴይነር ውስጥ እንዲገቡ መደረጋቸውንም ቤተሰቦቻቸው በሀዘን ተሞልተው ይናገራሉ፡፡

No comments: