Tuesday, November 8, 2016

ለምንድን ነው እርስ በእርስ እየተሻኮትን ለወያኔ እድሜ የምንጨምርለት?

የኢትዮጵያ ህዝቡ አንድ በሆነበት ሰዓት በፖለቲካው ድርጅቶች ርዕዮተዓለም መከፋፈል ምክንያት ህዝቡን ከጨቋኝ ስርዓት መታደግ ያልተቻለበት ግዜ ላይ መሆናችንን አስተውለናል ካላስተዋልን እናስተውል እንጂ! ዛሬ በዚህ ወሳኝ ትግል ምዕራፍ በሆንበት ወቅት ላይ ሆነን አንድነታችን ካልታየ ነገ ደግሞ እንደፈራነው ስንታገል የነበርነው ድርጅት እራስ በራሳችን መሻኮት ልንጀምር ነው ማለት ነው ኧረ ጠንቀቅ እንበል!!
ኢትዮጵያ ውስጥ የሐይማኖት፣ የፖለቲካ፣የጎሳ ችግርች ሲፈጠር እንደ እሳት አደጋ አላርም እየነፉና እየከነፉ መሮጥና ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣት ብቻ ግን መሆን የለበትም፡፡መፍቴውን ማበጀት ያስፈልጋል።መፍቴው ደግሞ ልዩነታችንን ወደ ኋላ ትተን ህዝባችንን መታደግ ነው መሆን ያለበት! ያለበለዚያ ‹‹በአህያ ቆዳ የተሰራ ቤት፣ ይፈራርሳል ‹‹ጅብ የጮኸ ዕለት...›› እንዳይሆን አንድነታችንም የዘይትና የውሃ አይነት እንዳይሆን ማንም ቢሄድ፣ ማንም ቢመጣ የማይነቃነቅና መሰረተ ፅኑ እውነተኛ ኢትዮጵያዊ ሆኖ እንዲዘልቅ ወደ ታች ወርደን እናጥብቀው፡፡
ለፖለቲካ ድርጅቶች እውነት ለኢትዮጵያ ህዝብ ቆመናል ካልን አንድ የሚያረገን፣ የምናብርበት ግዜ አሁን ነው። ከዚህ የከፋ የጭቆናና የአፈና ዘመን አታሳዩን! ለህዝባችን በአንድ ላይ እንቁም !ዛሬ ህውሃት በወንዝ ላይ የወደቀ ዛፍ በሆነበት ግዜ እኛ የወንዙን ውሀ መልቀቅ ሲገባን የሀሳብ ልዩነት ገደለን። የነፃነት ጉዞ መጨረሻው ያማረና ጣፋጭ ነች። ድል ነፃነት ለናፈቀው ለኢትዮጵያ ሕዝብ !!
ኢትዮጵያ በክብር ለዘላለም ትኑር !!!

No comments: