Friday, September 4, 2015

የኢህአዴግ ካድሬዎች መረጋጋት ተስኖአቸዋል

ነኅሴ ፳፰ (ሀያ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የአዲስ አበባ ኢህአዴግ ጽ/ቤት የመስተዳድሩን ካድሬዎች ገምግሞ ለአብዛኞቹ ዝቅተኛ ነጥብ መስጠቱን ተከትሎ እና ከ4 ሺ በላይ ሰራተኞች በወንጀል እንደሚጠየቁ መነገሩን ተከትሎ፣ የመስተዳደሩ የኢህአዴግ አባላት ከፍተኛ መረበሽ ውስጥ ገብተዋል። በዚህም የተነሳ መስተዳድሩ አገልግሎቶችን መስጠት አቁሟል በሚባልበት ደረጃ መድረሱን ምንቾች ገልጸዋል። "ምንም ስራ እየተሰራ አይደለም፣ ካደሬው በሙሉ ድንጋጤ ላይ ነው፣ ሹመትና ሽረቱን እየጠበቀነ ነው፣ በዚህም የተነሳ ስራ ቆሟል ብሎ መናገር ይቻላል" ሲል የመስተዳድሩ ሰራተኛ ተናግሯል። በርካታ ባለጉዳዮች እሮሮ እያሰሙ ቢሆንም፣ መፍትሄ የሚሰጥ አመራር በመጥፋቱ ፣ አዲስ ሹመት እስከሚሰጥ ድረስ ችግሩ ተባብሶ እንደሚቀጠል ምንጫችን ጠቅሷል። ኢህአዴግ አላማውን ደግፈው የሚታገሉ አባሎችን ለማግኘት እየተሳነው መምጣቱን በቅርቡ ባካሄደው ጉባኤ ገልጿል። አብዛኛው አባሎቹ አርሶ አደሮች መሆናቸውን የሚገልጸው ግንባሩ፣ ከአርሶ አደሩ ውጭ ያለው ደጋፊው አብዛኛው ለጥቅም ብሎ የቀረበው በመሆኑ፣ የድርጅቱን ህልውና አደጋ ላይ ጥሎታል። ግንባሩ ከመሞቱ በፊት የሞት ሽረት ትግል በማድረግ ችግሩን ለመቅረፍ መዘጋጀቱን ገልጿል። ምንም እንኳ ታች ያሉ በርካታ አባላት ሊባረሩ ወይም ወደ ተለያዩ ስራዎች ሊመደቡ ቢችልም፣ ቁልፍ ችግሩ ያለው ከዋና አመራሩና ከስርአቱ በመሆኑ ፣ ኢህአዴግ አሁን በሚወስደው እርምጃ ይህ ነው የሚባል ለውጥ አይመጣም ሲል ዘጋቢያችን አስተያየቱን አስፍሯል።

No comments: