Wednesday, January 22, 2014

በሰብአዊ መብት አያያዝ አደጋ ላይ የወደቀው የኢትዮጵያ ገፅታ አሁን ደግሞ ተባብሷል ይለናል Human Right Watch በ2014

በሰብአዊ መብት አያያዝ አደጋ ላይ የወደቀው የኢትዮጵያ ገፅታ አሁን ደግሞ ተባብሷል ይለናል Human Right Watch በ2014

በሰብአዊ መብት አያያዝ አደጋ ላይ የወደቀው የኢትዮጵያ ገፅታ አሁን ደግሞ ተባብሷል ይለናል Human Right Watch በ2014 የዓለም የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ሪፖርቱ፡-ኢትዮጵያ


ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እ.ኤ.አ በነሀሴ ወር 2012 ዓ.ም. መሞታቸውን ተከትሎ በኢትዮጵያ የተተካው አዲሱ አመራር ሰብዓዊ መብቶችን የሚመለከቱ ማሻሻያዎች እንደሚያደርግ ተጥሎ የነበረው ተስፋ ተዳፍኗል፤ በ2013 ዓ.ም ተጨባጭ የሆነ የፖሊሲ ለውጥ አልታየም፡፡ ይልቁንም የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ሃሳብን የመግለጽ፣ የመደራጀት እና በሰላም የመሰብሰብ ነጻነት ላይ የጣሉትን ጥብቅ ገደብ ማስፈጸማቸውን የቀጠሉበት ሲሆን የሲቪል ማህበራትን እና ነጻ መገናኛ ብዙሃንን እንቅስቃሴ ለማዳከም አፋኝ ሕጎችን ይጠቀማሉ፤ግለሰቦችንም ፖለቲካዊ መነሾ ያላቸውን ክሶች በመመስረት የጥቃት ዒላማ ያደርጋሉ። መንግስት በሃይማኖታዊ ጉዳዮቻቸው ላይ ጣልቃ መግባቱን የተቃወሙ ሙስሊሞች ዓመቱን ሙሉ በጸጥታ ሃይሎች የዘፈቀደ እስር፣ እገታ፣ ድብደባ እና ሌሎች ተገቢ ያልሆኑ አያያዞች ተፈፅሞባቸዋል፡፡ በሐምሌ ወር 2012 ዓ.ም. የታሰሩት 29ኙ የተቃውሞው መሪዎች የፍርድ ሂደት ከጥር ወር 2013 ጀምሮ ለህዝብ፣ ለመገናኛ ብዙሃን፣ እና ለቤተሰብ አባላት ዝግ ተደርጓል፡፡ እጅግ አወዛጋቢና መሠረታዊ ግድፈት ያለባቸውን ድንጋጌዎች በያዘው የሃገሪቱ የጸረ ሽብርተኝነት ህግ መሰረት ጥፋተኛ የተባሉ የተቃዋሚ መሪዎች እንዲሁም አራት ጋዜጠኞች አሁንም በእስር ላይ ይገኛሉ፡፡
ከሃገር ውስጥ በሚገኝ ገቢ እና ከውጭ በሚመጣ እርዳታ በሚደገፉ ስፋት ያላቸው የልማት ፕሮግራሞች አፈጻጸም ምክንያት የአንዳንድ ማህበረሰብ ተወላጅ ነዋሪዎች ያለበቂ ምክክር ወይም ምንም አይነት ካሳ ሳይከፈላቸው ከመኖርያቸው እንዲፈናቀሉ ይደረጋል፡፡ የጸጥታ ሃይሎች ነዋሪዎችን ከመኖሪያ ቀያቸው አንስተው ወደ ሌላ ቦታ ለማስፈር ሃይል፣ ማስፈራሪያ እና ዛቻ ይፈጸማሉ፤ ለምሳሌ በታችኛው የኦሞ ሸለቆ የሚገኙ ተወላጅ ነዋሪዎች ለዘመናት የኖሩበት መሬት መንግስት ለሚያካሂደው የስኳር መስኖ ልማት ይፈለጋል በሚል መፈናቀላቸው እንደቀጠለ ነው። በሰላም የመሰብሰብ ነጻነት ከ2012 ዓ.ም. ጀምሮ ከሀገሪቱ አጠቃላይ ህዝብ ቢያንስ 30 በመቶ የሚሆነውን ቁጥር የሚይዙት የኢትዮጵያ ሙስሊም ማህበረሰብ አባላት ተከታታይ ህዝባዊ ተቃውሞ አድርገዋል፡፡ የተቃውሞው መነሻ ምክንያት መንግስት በእስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ውስጥ እና በአዲስ አበባ በሚገኘው የአወሊያ መስጊድ ላይ ይፈጽማል የተባለውን ጣልቃ ገብነት በመቃወም ነው፡፡ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎቹን ለመግታት መንግስት ሃይል ተጠቅሟል፤ የዘፈቀደ እስር እና ድብደባ በተቃዋሚዎቹ ላይ ፈጽሟል፤ እነዚህ ሕገ ወጥ ተግባራት በሀምሌ 2012 ዓ.ም በቁጥጥር ስር ውለው በጥቅምት 2012ዓ.ም በጸረ ሽብርተኝነት አዋጁ መሰረት ክስ በተመሰረተባቸው 29 ታዋቂ የተቃውሞ እንቅስቃሴው መሪዎች ላይም ተፈጽመዋል፡፡ ከፍተኛው ፍርድ ቤት የፍርድ ሂደቱን መገናኛ ብዙሃንን፣ ዲፕሎማቶችን እና የቤተሰብ አባላትን ጨምሮ ህዝብ እንዳይከታተለው ከጥር ወር ጀምሮ ዝግ አድርጎታል፡፡ አንዳንዶቹ ተከሳሾች በእስር ላይ እያሉ ተገቢ ያልሆነ አያያዝ እንደተፈጸመባቸው ተገልጿል። እንዲሁም እንዳንዶቹ ተከሳሾች ለሁለት ወራት ያህል የሕግ አማካሪ ወይም ጠበቃ ያላገኙበት ሁኔታና ከቤተዘመድ ጋር ለመገናኘት የነበረውን ችግር ጨምሮ የፍርድ ሂደቱ በሕግ በተቀመጡ ስርዓቶች አግባብ መካሄዱን ጥያቄ ውስጥ የሚከቱ በርካታ ግድፈቶች ተፈጽመዋል።
በተከሳሾቹ ላይ በመንግስት ቴሌቪዥን ውንጀላ እና ክስ ያለበት መረጃ በማስተላለፍ መንግስት ተከሳሾቹ ከፍርድ ውሳኔ በፊት ነጻ ሆነው የመገመት መብታቸውን የሚጋፋ ድርጊት ፈጽሟል። መንግስታዊ በሆነው የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን (ኢቲቪ) ጃሃዳዊ ሃረካት የሚል ርዕስ ያለው ፕሮግራም በጥር ውስጥ የተላለፈ ሲሆን ፊልሙ ከተከሳሾቹ ውስጥ አምስቱ የፍርድ ሂደቱ ከመጀመሩ በፊት በቁጥጥር ስር እያሉ የተቀረጸ ክፍል አካቷል። ፕሮግራሙ የተቃውሞው መሪዎችን እንደ አሸባሪዎች በመቁጠር የሙስሊሞቹን የተቃውሞ እንቅስቃሴ ከአክራሪ የእስልምና ሃይሎች ጋር አነጻጽሯል፡፡ እስሩ እንዳለ ቢሆንም በ2013ም ተቃውሞው ቀጥሏል፡፡ በነሃሴ ወር መጀመሪያ ላይ በአዲስ አበባ እና በሌሎች ከተሞች የረመዳን ወር መጨረሻ የሆነው የኢድ አል ፈጥር በዓል በሚከበርበት ዕለት የተቃውሞ ሰልፎች ተካሂደዋል፡፡ የአይን እማኞች በአዲስ አበባ በርካታ ቁጥር ያላቸው ፖሊሶች ተሰማርተው እንደነበረ የገለጹ ሲሆን ታማኝ ምንጮች ደግሞ ሰልፈኞቹን ለመበተን ፖሊስ ከተገቢው በላይ ሃይል እንደተጠቀመ እና ለጊዜውም ቢሆንም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰልፈኞችን በቁጥጥር ስር አውሎ እንደነበር ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ተሳትፎ አዲስ መጭ የሆነው ሰማያዊ ፓርቲ በሰኔ ወር ሰላማዊ ሰልፍ አካሂዷል፤ ሰልፉ በስምንት ዓመት ጊዜ ውስጥ በተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ የተዘጋጀ የመጀመሪያው ሰልፍ ነው፡፡ የጸጥታ ሃይሎች የሰማያዊ ፓርቲን ጽህፈት ቤት ጥሰው በመግባት በርካታ ሰዎችን በማሰራቸውና የፓርቲውን ንብረቶች በመውረሳቸው ምክንያት ፓርቲው በነሀሴ ወር ሊያካሂድ አቅዶ የነበረው ሰልፍ ተሰርዟል። ሰማያዊ ፓርቲ ቀደም ብሎ ሰላማዊ ሰልፉን ለማካሄድ ለመንግስት አቅርቦ የነበረው ጥያቄ ተቀባይነት ሳያገኝ ቀርቶ ነበር። የዘፈቀደ እስር እና ጎጂ አያያዝ የዘፈቀደ እስር እና በእስር ቤቶች የሚደረግ ጎጂ አያያዝ ከፍተኛ ችግር መሆኑን ቀጥሏል፡፡ ተማሪዎች፣ የተቃዋሚ ጎራ አባላት፣ ጋዜጠኞች፣ የሰላማዊ ሰልፍ ተሳታፊዎች እና ሌሎችም የመሰብሰብ፣ ሃሳብን የመግለጽ እና የመደራጀት መብታቸውን መግለጽ የሚፈልጉ ሰዎች በየጊዜው በዘፈቀደ ይታሰራሉ፡፡
አብዛኛውን ጊዜ በፖለቲካ ምክንያት የሚያዙ ሰዎች ላይ በተለይም እነዚህ ሰዎች ከክስ ወይም ከፍርድ ሂደት በፊት በሚታሰሩበት እና ማዕከላዊ በመባል በሚታወቀው አዲስ አበባ በሚገኘው የፌዴራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ማዕከል ጎጂ አያያዝ ይፈጸማል፡፡ በሃይል በማስገደድ ከእስረኞች መረጃ፣ የእምነት ቃል እና ሃሳብ ለማውጣጣት እስከ ማሰቃየት የሚደርስ ጥቃት እና ሌሎች ጎጂ አያያዞች የሚፈጸሙባቸው አጋጣሚዎች ብዙ ናቸው። የተያዙ ሰዎች በተለይ ክስ ከመመስረቱ በፊት ብዙ ጊዜ የህግ አማካሪ እንዳያገኙ ይደረጋል፡፡ ያልተገባ አያያዝ የተፈጸመባቸው እስረኞች ፍርድ ቤት ሲቀርቡ ከፍርድ ቤቶች የሚያገኙት መፍትሄ እጅጉን ውሱን ነው፤ አንዲሁም እስር ቤቶች እና ሌሎች የማቆያ ቦታዎች በገለልተኛ መርማሪዎች በመደበኛነት እንዲጎበኙ አይፈቀድም፡፡ ከመንግስት ጋር ቀረቤታ ያለው የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የተወሰኑ እስረኞችን እና እስር ቤቶችን የጎበኘ ቢሆንም በማንኛውም ገለልተኛ የሰብዓዊ መብቶች ወይም ሌላ ድርጅት መደበኛነት ያለው የክትትልና የምርምራ ስራ አይሰራም። በሃምሌ ወር ወደ ኢትዮጵያ ተጉዞ የነበረው የአውሮፓ ፓርላማ የልዑካን ቡድን አባላት አስቀድሞ ፈቃድ ተሰጥቶአቸው የነበረ ቢሆንም አዲስ አበባ የሚገኘውን የቃሊቲ ማረሚያ ቤት እንዳይጎበኙ በባለስልጣናት ተከልክለዋል።
ሃሳብን የመግለጽ እና የመደራጀት ነጻነት በ2009 ዓ.ም የጸረ ሽብርተኝነት አዋጅ እና የበጎ አድራጎት ድርጅቶች እና ማህበራት አዋጅ ከወጡ በኋላ በኢትዮጵያ ሃሳብን የመግለጽ እና የመደራጀት ነጻነት በከፍተኛ ደረጃ ተገድቧል፡፡ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች እና ማህበራት አዋጁ በዓለም ላይ ካሉ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን ለመቆጣጠር ከወጡ በጣም አፋኝ ህጎች አንዱ ነው፡፡ በሰብዓዊ መብቶች፣ መልካም አስተዳደር፣ ግጭት አፈታት፣ እና የሴቶች፣ የህጻናት እና አካል ጉዳተኛ ሰዎች መብቶች ዙሪያ አድቮኬሲ የሚሰሩ ድርጅቶች ከጠቅላላ ገቢያቸው 10 በመቶ በላይ እርዳታ ከውጭ ምንጮች መቀበል እንደማይችሉ ይደነግጋል፡፡ በዚህ ሕግ ሳቢያ እጅግ መልካም ስም የነበራቸው የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ድርጅቶች ይሰሩ የነበረውን ስራ በከፍተኛ ደረጃ የቀነሱ ሲሆን ሌሎቹም ሰብዓዊ መብቶችን የሚመለከቱ ስራዎችን መስራት ጭራሹኑ አቁመዋል። በርካታ ታዋቂ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋቾች በተፈጠረባቸው ስጋት ምክንያት ሃገሪቱን ለቀው ተሰደዋል፡፡ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን በከፍተኛ የመንግስት ቁጥጥር ስር ይገኛሉ፤ እንዲሁም በርካታ ጋዜጠኞች ራሳቸው ላይ ቅድመ ምርመራ ያካሂዳሉ፡፡ መንግስትን በፅኑ የሚተቹ ድረ ገጾች እና ጦማሮች በመደበኛነት ይዘጋሉ እንዲሁም የውጭ ሬድዮ እና ቴሌቪዥን ስርጭቶች በተደጋጋሚ ይታፈናሉ። ለነጻ የሃገር ውስጥ ጋዜጦች የሚሰሩ ጋዜጠኞች የሚደርስባቸው ተከታታይ ጥቃት እና ማስፈራራያ እንደቀጠለ ነው።
የጸረ-ሽብርተኝነት አዋጁ የፖለቲካ ተፎካካሪዎችን ለማጥቃት፣ ነጻ ሃሳብን ለማፈን፣ እንዲሁም ጋዜጠኞችን ዝም ለማሰኘት ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ በሐምሌ ወር 2012ዓ.ም የሽብር ጥቃት ለመፈጸም በማሴር እና አሸባሪ ድርጅት ውስጥ በመሳተፍ በሚል በተከሰሰው ጋዜጠኛ እና ብሎገር እስክንድር ነጋ ፈንታ ላይ የተሰጠውን የ 18 ዓመት የእስር ቅጣት ጠቅላይ ፍርድ ቤት በግንቦት ወር 2013 እንዲጸና ወስኗል። እስክንድር ‘የፔን’ የመጻፍ ነጻነት ሽልማትን በ2012 ተሸልሟል፡፡ የፍትህ ጋዜጣ ጋዜጠኛ የሆነችው ርዕዮት ዓለሙ ገቤቦ በጻፈችው ጽሁፍ ምክንያት በጸረ ሽብር ህጉ በተጠቀሱ ሶስት ክሶች ተከሳ የጥፋተኝነት ውሳኔ ተሰጥቶባታል፡፡ በመጀመርያ ተፈርዶባት የነበረው 14 ዓመት በይግባኝ ወደ 5 ዓመት የተቀነሰላት ቢሆንም የቀረው የአምስት ዓመት ፍርድ ላይ ያቀረበችው ይግባኝ በጥር ወር ውድቅ ተደርጎባታል፡፡ ርዕዮት ከፍተኛ ዝና ያለውን የ2013 የዩኔስኮ ጉሌርሞ ካኖ የዓለም ፕሬስ ነጻነት ሽልማት ተሸልማለች፡፡ የሙስሊሙ ህብረተሰብ የሚያካሂዳቸውን የተቃውሞ ሰልፎችን ሲዘግቡ የነበሩ ጋዜጠኞች ማስፈራሪያ ደርሶባቸዋል እንዲሁም በዘፈቀደ ታስረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከህትመት ውጭ የሆነው የሙስሊሞች ጉዳይ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ የነበረው ሰለሞን ከበደ በጥር ወር የታሰረ ሲሆን የጸረ-ሽብር ህጉን አዋጅ በመጣስ ክስ ተመስርቶበታል፡፡ የጋዜጣው የቀድሞ ዋና አዘጋጅ ዩሱፍ ጌታቸው በ2012 በተመሳሳይ ህግ ተከሷል፡፡ ሌሎች በርካታ ጋዜጠኞች በ2013 ከኢትዮጵያ ተሰደዋል፤ ይህም ሃገሪቱን በስደት ላይ ባሉ ጋዜጠኞች ብዛት ከዓለም ሶስተኛ ሃገር አድርጓታል፡፡
ከልማት ፕሮግራሞች ትግበራ ጋር በተያያዘ የሚፈጸም በሃይል ማፈናቀል የኢትዮጵያ መንግስት ከሚያካሂደው የሰፈራ መርሃ ግብር ጋር በተያያዘ አንደሚፈፀሙ የሚገለጸውን በደሎች መንግስትም ሆነ የለጋሽ ማህበረሰብ አባላት በበቂ ሁኔታ መመርመር አልቻሉም፡፡ የመሰረታዊ አገልግሎቶችን አቅርቦት ለማሟላት በሚል ምክንያት በዚህ መርሃ-ግብር 1.5 ሚሊዮን የገጠር አካባቢ ነዋሪዎች ከመኖርያ አካባቢያቸው ተነስተው በሌሎች ቦታዎች እንዲሰፍሩ ተደርጓል፡፡ ይሁንና መርሃ ግብሩ ተግባራዊ በተደረገበት በመጀመሪያው ዓመት በጋምቤላ ክልል አንዳንድ ቦታዎች የተካሄደው ሰፈራ በሃይል የተደረገ ሲሆን ድብደባ እና የዘፈቀደ እስር የተፈጸሙባቸው አጋጣሚዎችም ነበሩ። ከዚህም ሌላ የማስፈሩ ስራ የተካሄደው ከተነሺዎቹ ጋር በቂ ምክክር ሳይደረግ እና በቂ የካሳ ክፍያ ሳይፈጸም ነው። የዓለም ባንክን የአሰራር ተጠያቂነት የሚከታተለውና ከባንኩ ነፃ የሆነው የቁጥጥር ቡድን በስደት ላይ የሚገኙ የአኙዋክ ብሔረሰብ አባላት ባንኩ ጋምቤላ ውስጥ የራሱን የአሰራር ሁኔታዎች ጥሷል በማለት ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ሙሉ ምርመራ እንዲደረግ በማለት ያቀረበውን የውሳኔ ሃሳብ የዓለም ባንክ ስራ አስፈጻሚ ዳይሬክተሮች ቦርድ በሐምሌ 2013 ተቀብሎታል። ይህ ሪፖርት በሚዘጋጅበት ወቅት ምርመራው በመካሄድ ላይ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ በታችኛው የኦሞ ሸለቆ የሚኖሩ 200 ሺህ ተወላጅ ነዋሪዎችን ከመሬታቸው ላይ በማስለቀቅ በ245 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የስኳር ልማት ስራ ማከናወኗን ቀጥላለች። እነዚህ በጥምር ግብርና እና ከብት እርባታ የሚተዳደሩ ተወላጅ ነዋሪዎች ለዘመናት ከኖሩበት መሬት ተፈናቅለው በሰፈራ መርሃ ግብር አማካኝነት በቋሚ መንደሮች እንዲሰፍሩ ተደርጓል።
ዋና ዋና ዓለምአቀፍ አካላት ኢትዮጵያ ከውጭ ለጋሾች እና ከአብዛኞቹ የቀጠናው ጎረቤቶቿ ጋር መልካም ግንኙነት አላት፡፡ ይህ ጠንካራ ግንኙነት የተመሰረተው ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ በመሆኗ፣ ለተባበሩት መንግስታት የሰላም ማስከበር ተልዕኮ በምታደርገው አስተዋጽኦ፣ ከምዕራብ ሃገራት ጋር በጸጥታ ጉዳይ ላይ ባላት ትብብር እና የተወሰኑ የሚሊኒየም የልማት ግቦችን በማሳከት ረገድ ባስመዘገበችው እድገት ምክንያት ነው፡፡ ሃገሪቷ ያላት ይህ ጠንካራ ግንኙነት የዓለም ዓቀፉ ማህበረሰብ ኢትዮጵያ በሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ ላይ ያለችበትን አሳሳቢ ሁኔታ በዝምታ እንዲያልፍ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ በ2013ም ኢትዮጵያ በሱዳን እና በደቡብ ሱዳን መካከል ያላትን የአደራረዳሪነት ሚና የቀጠለች ሲሆን ወታደሮቿም በአወዛጋቢው አቢዬ ግዛት የሰፈነውን አስተማማኝ ያልሆነ ጸጥታ በማስጠበቅ ተግባር ላይ ተሰማርተዋል። የኢትዮጵያ ወታደሮች ወደሶማልያ ዘልቀው መግባታቸውን የቀጠሉ ቢሆንም ወታደሮቹ በዚያ የተሰማራው የአፍሪካ ህብረት ሰላም አስከባሪ ሃይል አካል አይደሉም። ኢትዮጵያ ከፍተኛ መጠን ያለው ድጋፍ ከለጋሾች ማግኘቷን የቀጠለች ሲሆን በ2013 ያገኘችው ድጋፍ 4 ቢሊዮን ዶላር ይጠጋል፡፡ የኢትዮጵያ የልማት አጋሮች አንደመሆናቸው መጠን ለጋሽ ሃገራት እጅግ አስከፊ ሆነውን የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች አያያዝ ሁኔታ አስመልክቶ ግን ዝምታን መርጠዋል። ከልማት መርሃ ግብሮች አፈጻጸም ጋር በተያያዘ ተፈጽመዋል የተባሉ በደሎችን አስመልከቶ የሚቀርቡ ክሶችን ለመመርመር የሚወስዱት እርምጃም እጅግ ውሱን ነው።
ግብጻዊያን ኢትዮጵያ በምትገነባው ታላቁ የህዳሴ ግድብ ምክንያት ከናይል ወንዝ ከፍተኛ መጠን ያለው ውሃ ወደ ግድቡ ይቀየሳል የሚል ስጋት ስለገባቸው በ2013 ዓ.ም. የኢትዮጵያ እና የግብጽ ግንኙነት የበለጠ ሻክሯል። 85 በመቶ የሚገመተው የናይል ወንዝ ውሃ ምንጭ ኢትዮጵያ ስትሆን ግብጽ ደግሞ ለሚያስፈልጋት ማንኛውም የውሃ ፍላጎት ሙሉ በሙሉ በናይል ወንዝ ላይ ጥገኛ ነች፡፡ ግድቡ 6 ሺህ ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል በማመንጨት ከአፍሪካ ትልቁ የሃይድሮኤሌክትሪክ ፕሮጀክት ይሆናል፡፡ የግድቡ ግንባታ የተጀመረው በ2012 ሲሆን በ2018 ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል። ከምዕራባዊያን ለጋሽ ሀገራት በተጨማሪ ቻይና፣ ህንድ እና ብራዚል የተለያዩ ከፍተኛ መጠን ላላቸው የልማት ስራዎች የሚያደርጉት የገንዘብ ድጋፍ በየጊዜው እየጨመረ መጥቷል። ወደ ኢትዮጵያ የሚገባው የውጭ የግል ኢንቨስትመንት እየጨመረ የሚገኝ ሲሆን በ2013 የግብርና ንግድ፣ ሃይድሮኤሌክትሪክ፣ ማዕድን ማውጣት እና ነዳጅ ፍለጋ ኢንቨስትመንት ስራዎች በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመሩ ነው።የግብርና ንግድ ኢንቨስትመንት በዋናነት ከህንድ፣ ከመካካለኛው ምስራቅ እና በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን የሚመጡ ሲሆን የመሬት ዋጋው ዝቅተኛ መሆን እና ለጉልበት የሚከፈለው ዋጋ አነስተኛነት ባለሃብቶቹን የሚስብ ሆኗል። እንደ ሌሎቹ በርካታ ትልልቅ የኢትዮጵያ የልማት ፕሮጀክቶች ሁሉ እነዚህ መርሃ ግብሮች ሲተገበሩ ሰዎችን ከመሬታቸው በሃይል የማፈናቀል ተግባር ሊፈጸም ይችላል የሚል ከፍተኛ ስጋት አለ።

Tuesday, January 21, 2014

የደህንነት ሰራተኞች ሃላፊነታችን ለአገር ወይስ ለፖለቲካ ስርአቱ ነው የሚል ጥያቄ አነሱ

የደህንነት ሰራተኞች ሃላፊነታችን ለአገር ወይስ ለፖለቲካ ስርአቱ ነው የሚል ጥያቄ አነሱ

esat

ጥር ፱ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-መንግስት በመረጃዎች አያያዝ ዝርክርክነት ፣ በሳይበር በሚደረጉ ስለላዎች እና ከውስጥ ባሉ የመንግስት አካላት እየሾለኩ በሚወጡ መረጃዎች ህልውናየ አደጋ ላይ ወድቋል በማለት ግመገማ ማድረጉን ተከትሎ  ”የደህንነት ሰራተኞች ሃላፊነታችን ለማን ነው?” የሚል ጥያቄ ማንሳታቸውን  ከደህንነት መስሪያ ቤት ለኢሳት የደረሰው በድምጽ የተደገፈ መረጃ አመለከተ። በስብሰባው ላይ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እና የመንግስት ሹሞችም ተገኝተው ነበር።
ጥያቄውን ያነሱት በፌደራል ስር የሚገኙ የደህንነት ስራተኞች እና ቀደም ብሎ በአቶ መለስ ዜናዊ ዘመን በትግራይ ውስጥ በመቀሌ ዩኒቨርስቲ ሽፋን የተቋቋመው ኤም አይ ቲ እየተባለ በሚጠራው ከመቀሌ ከተማ 9 ኪሎሜትር ርቀት ላይ በተገነባው ተቋም ውስጥ ተመርቀው የወጡት የደህንነት ሰራተኞች ናቸው።
የደህንነት ሰራተኞቹ “የእኛ ሃለፊነት የአገር ደህንነትን ማስጠበቅ ነው የፖለቲካ ስርአቱን ?” በሚል  ጥያቄ ያነሱ ሲሆን፣ አንድ  የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣን  ” የፖለቲካ ስራ የማይሰራ ደህንነት የለም፣ የደህንነት ስራ ሲጀመር ስርአት የማቆየት ስራ ነው፤ ስርአቱን የምናቆይበት ደግሞ ፕሮፌሽናል ነው፣ በስርአቱ ላይ እምነት ማሳደር የሚጠይቅ ተግባር ነው፣ የግንቦት7ትን አስተሳሰብ የሚያቀነቅንና ስርአቱ በጉልበት መፍረስ አለበት ብሎ የሚያስብ ሰው፣ የተስፋየ ወልደ ስላሴ አይነት የደህንነት ብቃት አለው ቢባል፣ ሞሳድ 20 አመታት አሰልጥኖታል ቢባል ስርአቱን ከማፍረስ ውጭ ደህንነቱን ሊያስጠብቅ አይችልም” ፣ ስለዚህ የደህንነት ስራ ለሚሰሩ ወገኖች የፖለቲካ ወገንተኝነታቸው ወሳኝ ነው የሚል መልስ ሰጥተዋል ።
“የደህንነት ተቋሙ ፣ ሰራዊቱና ሚዲያው በተቃዋሚዎች ዘንድ መቼውንም ቢሆን ገለልተኛ ተደርጎ አይቆጠርም” ያሉት እኝህ ከፍተኛ ባለስልጣን ፣ ገለልተኛ ማድረግ የሚባል አስተሳሰብ ያለው ካለ እንደዛ ሊሆን አይችልም፣ ሊሆን የሚችለው የተቃዋሚዎችን ሰዎች ደህንነት ውስጥ ማስገባት ነው ብለዋል። ” በተለይም በተቋም ደረጃ ፤በምህጻረ ቃል ኢንሳ እየተባለ የሚጠራው የመረጃ ደህንነት መስሪያ ቤት፤ የዜግነት እና ኤምግሬሺን ፤የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፤በጀኔራል ሳሞራ የኑስ የሚመራው የመከላከያ ደህንነት ፤የአስተዳደር እና ፀጥታ ፤ የፌደራል ፖሊስ ፤ የፀረ ሽብር ግብረ ሃይል በእዝ ሰንሰለት በሚፈጠር ልዩነት እርስ በርስ እየተወዛገቡ ሲሆን፣ ተቋሞቹን በትክክል የሚመሩትን አካላት  ለመለየት አስቸጋሪ ሆኖ መገኘቱና እርስ በርስ በሚፈጥሩት  እሰጥ አገባ  አንዱ አንዱ የሚሰራውን የማጠፋፋት እርምጃ እየወሰዱ መሆኑ በግምገማው ላይ ተነስቷል፡፡
የመንግስት ሚስጥሮች ለሶስተኛ ወገኖች ተላልፈው እየተሰጡ በመሆኑ ሚስጢሮችን  መደበቅ የማይቻልበት ደረጃ ላይ ተደርሷል ሲሉ አንዳንድ ባለስልጣኖች አስተያየቶችን ሰጥተዋል።
ለተነሱት አስተያየቶች መልስ የሰጡት ባለስልጣኑ፣ ኢንሳ የተቋቋመውም ይህን ለመስራት መሆኑን  ገልጸው፣ “አገሮች ሙሉ በሙሉ ከሳይበር ስለላ ነጻ ባለመሆናቸው አቶ ሃይለማርያምም ነጻ ናቸው ብየ አላስብም” ብለዋል። “አሜሪካኖች የምንናገረውን ሁሉ ከፈለጉ ይሰሙታል” የሚሉት እኝሁ ባለስልጣን፣ “እኛም የአቅማችንን ያክል አሜሪካኖች የሚናገሩትን ለማዳመጥ እንሞክራለን” ብለዋል። የሳይበር ስለላ ለማካሄድ ጥሩ ጅምሮች ቢኖሩም፣ ያን ያክል የምንኩራራበት ግን አይደለም በማለት ኢነሳ ያለበትን ደረጃ አመላክተዋል
ከኦሮሚያና ከደቡብ የመጡ የደህንነት ሹሞች ደግሞ “በመከላከያ የደህንነት ተቋሞች ውስጥ የአንድ ብሄር የበላይነት ጎልቶ ይታያል” በሚል ቅሬታ ያነሱ ሲሆን ፣ ባለስልጣኑም “የሰራዊት ማመጣጠን ስራ በረጅም ጊዜ የሚሰራ ስራ  ነው ” በማለት ለመመለስ ሞክረዋል።
” ትግሉን መርተው እዚህ ድረስ የመጡ ሰዎችና በመከላከያ ውስጥ ያለውን የመኮንኖች ቦታ የያዙት ከአንድ አካባቢ የመጡ መሆናቸው ግልጽ ነው የሚሉት ባለስልጣኑ፣ ያም ሆኖ ከትግራይ የመጡ በርካታ ጄኔራሎች ጡረታ እንዲወጡ ቢደረግም ሂደቱ ግን ረጅም ጊዜ የሚወሰድ ነው ሲሉ አክለዋል።
“የብሄር ተዋጽኦ ብቻ የአንድን ሰራዊት ጠንካራና ደካማ ጎን መገለጫ ተደርጎ መወሰድ ካለበት አደጋ አለው ” ያሉት ባለስልጣኑ፣ የአንድ ብሄር የበላይነት አለ ተብሎ በአጭር ጊዜ ለማመጣጠን ብቻ በአንድ አዳር ሁሉንም ነገር መቀየር እንደማይቻል መንግስት ያምናል ሲሉ ተናግረዋል
አቶ መለስ ዜናዊ በውጭ ሃይሎች ተገድለዋል ይባላልና በምን እንደሞቱ በትክክል ይነገረን በሚል ባለስልጣናት ላነሱት ጥያቄም የደህንነት ባለስልጣኑ፣ “አቶ መለስ በውጭ ሃይሎች ተገድለዋል የሚል ትክክለኛ ማስረጃ የለም በማለት መመለስ የጀመሩት ባለስልጣኑ፣ እርሳቸው የሞቱት በስራ ብዛት ተዳክመው እና ህክምናውን መቋቋም ባለመቻላቸው ነው ሲሉ ደምድመዋል።
በተያያዘ ዜናም የሃገሪቱን ደህንነት አደጋ ላይ ለመጣል ከኢሳት ጋር በመሆን እየሰራችሁ ነው፣ ለኢሳትም መረጃ ታቀብላላችሁ  ተብለው የተጠረጠሩ  5 የደህንነት አባላት በቁጥጥር ስር ውለዋል።  ወጣት መብራቴ ታምራት ፤ወጣት ጀማል አወል ፤ወጣት ደጀኔ አድማስ ፤ ወጣት ሃይሉ ጨርቆስ ፤መቶ አለቃ አሰፋ አብርሃ ሰሞኑን በደህንነቶች ቁጥጥር ስር መዋላቸውን የኢሳት የደህንነት ምንጮች ገልጸዋል።
በተመሳሳይ ዜናም በሃገሪቱ በ28ቱ ዩኒቨርስቲዎች የሚገኙ የህወሃት አባላት ተማሪዎች እና የደህንነቶች ሃለፊዎች ግምገማ መጀመራቸውን ለማወቅ ተችሎአል።
በግምገማው ወቅት የኦህዴድ እና የብአዴን መሪዎች የተማሪዎችን እንቅስቃሴ በመከታተል ባሰዩት ውጤት የተገመገሙ ሲሆን፣ ባለፉት ስድስት ወራት የአክሱም ፤ ደብረ ታቦር እና ደብረ ብርሃን የኒቨርስቲዎች ከፍተኛ የአመጽ እንቅስቃሴ የታየባቸው በመሆኑ ልዩ የደህንነት ክትትል እንደሚያስፈልጋቸው ተወስቷል።

Saturday, January 18, 2014

ሰበር ዜና!!!

መንግስት በነገው ጥምቀት በአል ላይ በሙስሊሙና 

ክርስትያኑ መካከል ግጭት ለመቀስቀስ ማሴሩን ምንጮች 

ገለፁ!!!


 ቅዳሜ ጥር 10/2006 መንግስት በነገው  የጥምቀት በአል በህዝበ ሙስሊሙ እና 

በክርስትና ሃይማኖት ተከታይ ወንድምና እህቶቻችን መካከል ግጭት ለመፍጠር 

በማሴር ላይ እንደሚገኝ ምንጮች ገለፁ። ጥቃቱ ሊፈፀም የታሰበው በሐይቅ፣ 

በአርሲ፣ በአላባ ቁሊቱ እና በሌሎች የክልል ከተሞችም ላይ ሲሆን የሙስሊም 

ልብስ የለበሱ ግለሰቦች በጥምቀተ በአል ላይ ህዝበ ክርስትያኑ ላይ ጥቃት 

እንዲፈፅሙ በማድረግ መሆኑንና በተመሳሳይም መስጊዶች ላይ ተመሳሳይ ጥቃት 

ባልታወቁ ግለሰቦች እንዲፈጸም መታሰቡንም ምንጮች ጨምረው ገልፀዋል። 


መንግስት ለዚህ እኩይ አላማው እንዲረዳው በዛሬው ምሽት በኢቲቪ በሃይማኖቶች 


መካከል ግጭት ለመቀስቀስ ያለመ ዘጋቢ ፊልም ያቀረበ ሲሆን በነገው እለት 

ሊፈጠር የሚችለውን ግጭት ሰበብ በማድረግም ለፖለቲካዊ ፍጆታው ሊያውለው 

በማሴር ላይ ይገኛል። ይህን መሰል እኩይ ሴራ ከአንድ አገር አስተዳድራለሁ ከሚል 

መንግስት የማይጠበቅ እጅግ ሀላፊነት የጎደለው ተግባር መሆኑ እሙን ነው። 

በመሆኑም ህዝበ ሙስሊሙ ከማንኛውም ሁከት ፈጣሪ ተግባር በመቆጠብና 

መረጃውንም ላልሰሙ ወገኖቻችን ሁሉ በማዳረስ ሴራውን እንዲያከሽፍ፣ እንዲሁም 

የተለመደውን ከሌሎች ሃይማኖቶች ተከታይ ወገኖች ጋር በሰላምና በመከባበር 

የመኖር አኩሪ ልምዱን እንዲቀጥል ጥሪ እናቀርባለን! የመንግስትን ግጭት የመቀስቀስ 

ሴራ ተባብረን እናክሽፍ! 



ድምጻችን ይሰማ!

ዛሬ የሚያስፈሯሯችሁን እስከ ዘላለሙ የማትሰሙበት ግዜ ይመጣልና አትፍሩ

ዛሬ የሚያስፈሯሯችሁን እስከ ዘላለሙ የማትሰሙበት ግዜ ይመጣልና አትፍሩ


ህወሃት የሚያራምደው የዘረኝነት ፖለቲካና፤ የተዘፈቀበት የሙስና አዘቀት ሊወጣ ከማይችልበት አዙሪት ውስት ከተውታል።ከእንግዲህ ወዲህ ለህወሃቶች የቀራቸው አንድ አማራጭ ብቻ ነው። ሁሉንም ዜጎች በዘረኝነት ሰንሰለት አስሮ ቀጥቅጦ እና አፍኖ መግዛት ቀጣዩ ቅዥታቸው ነው።
የዚህ አፍኖ የመግዛት ቅዥታቸው መገለጫም ዜጎች ህወሃት ስለሚፈፅመው ወንጀል ምንም ዓይነት መረጃ እንዳያገኙ ማድረግ አንዱ ነው።ህወሃት የሚፈፅመው ወንጀል ከህዝብ ዓይንና ጆሮ ተሠውሮ እንዲረሳ ይመኛል። ይሄን ምኞቱን እውን ለማድረግም ሌሎች ነፃ ሚዲያዎችን አሸባሪ ማለት ወይም ደግሞ ሌላ የተሰወረ አጀንዳ ያላቸው እያለ ማላዘንን ሥራየ ብሎ ተያይዘውታል። ከሰሞኑ አዲስ አበባ ውስጥ የሚታተሙ ስምንት የግል ህትመቶችን አሸባሪዎች በማለት ክስ መስርተዋል። አስቀድመው ፈርደው ከጨረሱ በኋላ ክስ መመሥረት የህወሃቶች የተለመደ የፍትህ ሥርዓት ነው። በአገሪቷ ታሪክ ውስጥ ለመጀመሪያ ግዜ ከመንግስት ቁጥጥር ውጪ ሁኖ የተቋቋመውን ኢሳትንም አሸባሪ እያሉ ሰሚ አልባ ጩኸት እየጮኹ ነው። የኢሳት ቴሌቭዥንና ሬዲዮንን የሚሰማም በአሸባሪነት ይከሰሳል እያሉ በየዜጎች ደጅ እየተንከላወሱ ለማስፈራራት እየሞከሩ ነው።
እኛ ግን እንዲህ እንላለን !!! አትፍሩ ! አትፍሩ ! አትፍሩ ! ኢሳትን ሰምታችኋል ብሎ የሚያስፈራሯችሁን ለዘላለሙ የማትሰሟቸው ግዜ እየመጣ ነው። የነፃነት ጎህ ቀዶ ሁላችን የፈለግነውን ሰምተን፤ ያልፈለግነውንም የምንተውበት ዘመን እሩቅ አይደለም። ግንቦት ሰባት የፍትህ የነፃነት እና የእኩልነት ንቅናቄም የተቋቋመው ዜጎች ያለማንም ጣልቃ ገብነት የወደዱትን ወስደው፤ የጠሉትን መተው የሚችሉበትን መንገድ ለማመቻቸት ነው። ዘረኞቹ በደምና አጥንት ታውረው ጭካኔን ከጀግንነት ቀላቅለው እኛ ብቻ ወንድ ባሉበት መንደር ሌላ ጀግና ኢትዮጵያዊ ወንድ ገስግሶ የሚመጣበት ዕለት እየደረሰ ነውና እንዳትፈሩ እንመክራችኋለን። ህወሃቶች ዜጎችን ከሰው በታች አድርገው ለመግዛት እንዲመኙ ያደረጋቸው እብሪት የሚተነፍስበት ዘመን እሩቅ አይሆንምና አሁንም አትፍሩ።
ህወሃቶች ከእነርሱ ቁጥጥር ውጪ ያሉ ነፃ ሚዲያዎችን እንደማይታገሱ የታወቀ ነው። ለምን ቢሉ የወንጀላቸው ብዛት፤ የክፋታቸው ጥልቀት ሳይነገር ተሠውሮ እንዲቀር ስለሚመኙ ነው። ይህን ምኞታቸውን እውን ለማድረግም ራሳቸው የሠረቱን ህግ ውልቅልቁን አውጥተው ያፈራርሱታል። ዜጎች መረጃ የማግኘት መብት አላቸው ተብሎ እነርሱ “ህገ-መንግስታችን” እያሉ በሚጠሩት ላይ በማያሻማ ሁኔታ የተቀመጠ ቢሆንም እነርሱ ግን ለራሳቸው ህግ መታመንን አልመረጡም። እንዲያውም እነርሱ ሞተንለታል የሚሉትን ህግ አፈር አስገብተው ራሳቸው ህግ ሆነው ተፈጥረዋል። እነርሱ ህግ ሁነው በመፈጠራቸውም በየዜጎች ደጅ እየተንከላወሱ ኢሳትን ብትሰሙ ወዮላችሁ እያሉ ያስፈራራሉ። ዜጎች ግን የሞኝ ዘፈናቸውን መልሰው መልሰው ለሚያላዝኑ ኢሕአዴጋዊያን ዛቻ የሚንበረከኩ አይሆኑም። አገራቸውን በተመለከተ ማንኛውንም መረጃ ለመስማት ያላቸውን ነፃነትም ለምናምንቴዎች አሳልፈው የሚሰጡ አይሆኑም።
ጎሬቤታችን ኬኒያ ከአስር በላይ የግል ቴሌቭዥን ጣቢያዎች አሏት።በርካታ በአጭር ሞገድና በኤፊኤም ሞገዶች የሚተላለፉ ሬዲዮኖችም አሏት። የኬኒያ መንግስት ለዜጎቹ ክብርና ፍቅር ስላለው የተቻለውን ያክል ነፃ ሚዲያ እንዲኖር ይጥራል። ለህዝቡ ክብርና ፍቅር የሌለው ህወሃት ግን በወረቀት ላይ በፃፈው ህግ ዜጎች መረጃ የማግኘት መብታቸው ያልተገደበ ነው ቢልም በተግባር ግን የዜጎችን መረጃ የማግኘት መብት ያፍናል። ነፃ ሚዲያ እንዳይፈጠር ለማድረግ፤ የተፈጠሩትንም ለማጥፋት ግዜውንና የአገሪቷን ሃብት በከንቱ ያባክናል። ህወሃት ከድሃ ጉሮሮ እየነጠቀ ኢሳትን ለማፈን በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር አባክኗል። የአገሪቷ የህግ ተቋማትም ሌቦችንና ነፍሰ ገዳዮችን መከታተል ትተው በነፃነት እንፃፍ ብለው የተነሱ ጋዜጠኞችን በማሳደድ የአገሪቷን የሥራ ሠዓትና ሃብት በከንቱ ያባክናሉ። ህወሃቶች ይሄው ናቸው። አገር፤ ወገን፤ ህዝብ የሚባል ነገር በሂሊናቸው ያልተፈጠረ፤ እነርሱ ብቻቸውን ሌላውን ተጭነው መኖር የሚፈልጉ፤ የጨካኞችና የእብሪተኞች ስብስብ መሆኑን መዘንጋት አያስፈልግም።
የተከበራችሁ ያገራችን ዜጎች !
አገራችሁን በተመለከተ መረጃ ማግኘት የዜግነት መብታችሁ መሆኑን እንዳትረሱ። ይሄም እነርሱ “ህገ-መንግስት” ብለው በሚጠሩት ላይም በግልፅ ተቀምጧል። ይሄን በህግ ደንግጎ ሲያበቃ ኢሳትንና ሌሎችን ነፃ ሚዲያዎችን መስማት አትችሉም ሲል የማውቅላችሁ እኔ ነኝና የምትሰሙትንና የምታዩትን የምመርጥላችሁ እኔ ነኝ እያለ መሆኑን አስታወሱ። ይሄ ማለት አዋቂው እኔ እንጂ እናንተማ ክፉን ከደጉ ለመለየት ገና አልደረሳችሁም ማለት መሆኑንም መገንዘብ ያስፈልጋል።መንግስት ነኝ ብሎ በአገሪቷ ጫንቃ ላይ የተቀመጠው ህወሃት-ኢሕአዴግ ህዝቡን የማያከብር ብቻ ሳይሆን ለህዝብ ያለው ንቀትም ወሰን የሌለው ሁኗል። ይሄ ዘረኛና ዘራፊ ቡድን ክብራችንን አዋርዶና አንገታችንን አስደፍቶ ሊገዛን አይገባውም። ፍርሃት ይብቃ። ህወሃት እየፈጠረ ያለው ፍራቻን መሸሸ አይገባም፤ ይሄን ፍርሃት መጋፈጥ የጀግና ተግባር ነውና ለክብራችሁና ለነፃነታችሁ ስትሉ ፍርሃቱን ተጋፈጡት እንጂ አትሽሹት።
በዚያ በጨካኞች መንደር ሁናችሁ በሠላማዊ ትግል ብቻ ለውጥ እናመጣለን ብላችሁ የተደራጃችሁ የፖለቲካ ድርጅቶችም መረጃ የማግኘት፤ መረጃ የመሰብሰብ እና የማሰራጨት መብታችሁ ነው ብለን ልንነግራችሁ አንዳዳም። በነፃ ሚዲያ መናገርም ሆነ ለማንኛውም ሚዲያ መረጃ የመስጠት ማንም የሚሰጣችሁ መብት እንዳልሆነ ታውቃላችሁ። እኛ እንደምንገምተው ኢሳትም ሆነ ሌሎች ነፃ ሚዲያዎች የእናንተም ሃብት ናቸው። ህወሃት-ኢሕአዴግ አትስሙ ወይም ደግሞ አትናገሩ ሲላችሁ ያንን የእብሪተኛ ትዕዛዝ አለመቀበላችሁን ለነፃ ሚዲያዎች መረጃ በመስጠትና ሃሳባችሁን በነፃው ሚዲያ በመግለፅ እምቢተኝነታችሁን በማሳየት ለምትመሩት ህዝብ አርአያ እንድትሆኑ ብናሳስባችሁ ደፈሩን እንደማትሉ ተስፋ እናደርጋለን። ከዚህ አንፃር ሰማያዊ ፓሪትና አንድነት ያወጡትን መግለጫ በአድናቆት የምንመለከተው መሆኑን ለማስታወቅ እንወደላን።
ለህወሃት-ኢሕአዴጎች !
ራሳችሁን ከአሸባሪ ምግባርና መዝገብ ማስፋቅ ሳትችሉ የነፃነት ፍላጎት ያላቸውን ሁሉ አሸባሪ እያላችሁ ማላዘናችሁን የምታቆሙበት ግዜ እየመጣላችሁ ነው። እናንተ ከላይ ሁናችሁ ህዝቡ ከሥር ሁኖ እናንተን ተሸክሞ ለዘላለም እንደማይኖር አበክረን ልናሳውቃችሁ እንወዳለን።በየሰው ደጅ ካድሬዎቻችሁን ልካችሁ ኢሳትን አትስሙ እያላችሁ የማስፈራራት እብሪታችሁ ረገብ የሚልበት ግዜ እየመጣላችሁ ነው። ዛሬ ህዝባችንን የእኛን ብቻ ስሙ፤ የእነርሱን አትስሙ ማለታችሁ ለህዝባችን ያላችሁን ንቀት የሚያመላክት ነው።ህዝባችንን እንደናቃችሁና እንዳዋረዳችሁ አትቀጥሉም። የነፃነትን ፍላጎት አፍናችሁ አታቆሙትም። የፍትህ ጥማታችንን በአፈሙዝ ልትገቱት አትችሉም። የእኩልነትን ጥያቄ በውሸትና በዛቻ አታዳፍኑትም። እውነት እውነት እንላችኋለን ወንጀላችሁ ሳይነገር፤ በስውር የዘረፋችሁት በአደባባይ ሳይገለጥ አይቀርም። እኛም ቀንና ማታ ለዚያ ግብ ሳናገራግር እየሰራን ነው። በአገራችን የነፃነት ጎህ ሳይቀድ ለሽፋሽፎቶቻችን እንቅልፍ፤ ለስጋችንም ዕርፍት አይሆንም። የዘረኞችና የዘራፊዎች ጀንበር ሳትጠልቅ፤ የእኩልነት ናፋቂዎች ጎህ ሳትቀድ አናርፍም። ያነገታችሁት መሣሪያ የሸንበቆ ምርኩዝ እስከ ሚሆን የጀመርነውን ትግል ዕለት ዕለት እያጎለበትነው እንቀጥላለን።
ህወሃት-ኢሕአዴጎች ሆይ ስሙ! ይሄን ህዝብ ከሚችለዉ በላይ ገፍታችኋታል። ህዝቡም ሊሸከማችሁ ከሚገባ በላይ ተሸክሟችኋል።እንዲህ ህዝባችንን መፈናፈኛ አሳጥታችሁ እና እስከ ልጅ ልጆቻችሁ ረግጣችሁ ለመግዛት ያለማችሁት ህልም በህልምነቱ ብቻ እንደሚቀር ቅንጣት ታክል ጥርጣሬ አይግባችሁ። ትግላችን ጥሩ መሠረት ይዟል። ከዚህ በኋላ ወደ ኋላ የሚመልሰን ምድራዊ ኃይል የለም።እውነት እውነት እንላችኋለን ለዘላለም ኢትዮጵያዊያንን አዋርዳችሁ የመግዛት ህልማችሁ ቅዥት መሆኑን ደግመን ልንነግራችሁ እንወዳለን።
በህወሃት-ኢሕአዴግ ውስጥ ሁናችሁ የነፃነት፤ የፍትህ እና የእኩልነት ጥያቄያችንን የምትጋሩን ወገኖቻችን እሰክ አሁን የምታደርጉት የውስጥ ትግል ፍሬ እያፈራ ነው። ፍሬውን በራሪ ወፍ እንዳይለቅመው የተለመደው ጥንቃቄ እንዳይለያችሁ ይሁን። አሁን ህዝቡ መረጃ እንዳያገኝና፤ መረጃ እንዳይሰጥ የሚሞከረው ሙከራ ህገ-መንግስት ተብየውን የሚጥስ መሆኑን ታውቃላችሁ። ይሄን ካድሬው ሁሉ እንዲገነዘበው የውስጥ ትግሉ ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል። ራሱ ያወጣውን ህገ መንግስት አፈራርሶ ከትቢያ የሚቀላቅል ቡድን በምን ሞራል ብቃት ነው ሌላውን ህገ-መንግስቱን ሊንዱ ነበር እያለ የሚከሰው ? በኢትዮጵያዊያን ላይ የተጫነው ህገ-መንግስት በህወቶች ሲፈርስ ትክክል ፤በሌላው በተግባር እንዲውል ሲጠየቅ ደግሞ ስህተት ሁኖ በአሸባሪነት የሚያስከሥሥ መሆኑን ግንዛቤ መጨበጥ ይጠቅማል።
በመጨረሻም በህወሃት-ኢሕአዴግ የጭቆና ቀንበር ሥር ለምትንገላቱ ወገኖቻችን ሆይ ! አትፍሩ። ይህን የሚያስፈራራችሁን አካል እስከ መጨረሻው የማትሰሙበት ዘመን እየመጣ ነው። አሁን ፍርሃታችሁን ግደሉት።የምትሰሙትንና የምታዩትን እኔ ነኝ የምመርጥላችሁ ከሚል እብረተኛ እጅ ራሳችሁን ለማላቀቅ የግንቦት ሰባት ንቅናቄ እያደረገ ያለውን የነፃነት፤ የፍትህና የእኩልነት ትግል ተቀላቀሉ።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!!

ከኢሳት ጋር በተያያዘ የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣናት እየተወዛገቡ ነው

ከኢሳት ጋር በተያያዘ የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣናት እየተወዛገቡ ነው

ጥር ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- የኢህአዴግ ከፍተኛ ባለስልጣኖች ለኢሳት መረጃ በመስጠት ድርጅቱን ከውስጥ ሆነው የሚቦረቡሩ ሃይሎች አሉ በማለት እርስበርስ መወዛገባቸውን የደረሰን መረጃ አመልክቷል። አቶ በረከት ለሚኒስትሮችና ለኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች ያደረጉት ንግግር በኢሳት ከተለቀቀ በሁዋላ የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች እርስ በርስ እየተወነጃጀሉ ነው። የኢህአዴግ አንዳንድ ከፍተኛ አመራሮች ውስጣችን ማጥራት አለብን በሚል ትናንትና ዛሬ ለአመራሮች ማስጠንቀቂያ ሲሰጡ ውለዋል። ኢሳት ተጨማሪ መረጃዎችን በሰኞ ዘገባው ያቀርባል።

የአማራ ክልል የድርጅት ጉዳይ ሃላፊዎች ከአሸባሪዎች ጋር ግንኙነት ይኖራቸል ብለው የሚጠረጥሩትን ሁሉ እንዲይዙ ታዘዙ : ኢሳት ዜና

የአማራ ክልል የድርጅት ጉዳይ ሃላፊዎች ከአሸባሪዎች ጋር ግንኙነት ይኖራቸል ብለው የሚጠረጥሩትን ሁሉ እንዲይዙ ታዘዙ : ኢሳት ዜና

ጥር ፱ (ዘጠኝ) ቀን ፳፻፮ ዓ/ም ኢሳት ዜና
ባለፈው ወር በአማራ ክልል ርዕሰ ከተማ ባህርዳር የተካሄደውን የብአዴን እና የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች ስብሰባ ላይ የተላለፈውን ውሳኔ ተከትሎ የዞን እና የወረዳ የድርጅት ጉዳይ ሃላፊዎች ኢህአዴግ አሸባሪ እያለ ከሚጠራቸው የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር  በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ግንኙነት ይኖራቸዋል ተብሎ በሚጠረጠሩት ወጣቶች ላይ  የቁጥጥር ዘመቻ እንዲካሄዱ ትእዛዝ ተላልፎላቸዋል።
ጥር 8፣ 2006 ዓም በሁሉም የአማራ ክልል ወረዳዎች በተደረገው የብአዴን ስብሰባ ላይ ወጣቶች መረጃ በማስተላለፍ እና ለአሸባሪዎች መሳሪያ የሚሆኑ ሰዎችን በመመልመል ላይ በመሆናቸው  የግንኙነት ሰንሰለቱን ለመበጠስ አባላቱና አመራሩ ጠንክረው መስራት እንደሚገባቸው ተገልጾላቸዋል። እያንዳንዱ አባል በአሸባሪዎች ፕሮፓጋንዳ ሳይዘነጋ ጠንክሮ እንዲሰራም ትእዛዝ ተላልፎለታል።
“ከየትኛውም የሀገሪቱ ክልል ወጣቶች ባላይ የአማራ ክልል ወጣቶች ከአሸባሪዎች ጋር ግንኙነት እንዳላቸው መረጃ አለኝ” ያለው ኢህአዴግ በክልሉ እነዚህን ወጣቶች የመቆጣጠርና የመከታተል ዘመቻ በዘርፈ ብዙ ስልቶች ታጅቦ መካሄድ እንዳለበት አሳስቧል።
“በመሰረተ ቢስ አሉባልታዎች ከኢህአዴግ የኮበለሉና ወስጣቸው የሸፈተ የብአዴን አባላትም ሀቁን ተገንዝበው ከኢህአዴግ ጋር እንዲቀጥሉና ሀገሪቱን ወደ ላቀ እድገት እንዲያሸጋግሩ የድርጅት ጉዳይ ሀላፊዎች በስብሰባው ላይ ተናግረዋል፡፡
የመወያያ አጀንዳዎች ትምህርትና የመኖሪያ ቤት ሊዝ ጉዳይ ቢሆኑም የስብሰባው ውሎ ግን ከአጀንዳዎች ውጭ አሸባሪዎች በሚሏቸው አካላት ላይ ነበር ያሉት ስማቸው እንዳይገለፅ የፈለጉ የድርጅት አባላት፣  መንግስት በመኖሪያ ቤት ሊዝ ያቀረበው ጉዳይ ግን ከፍተኛ ተቀዋውሞ አስነስቷል ብለዋል፡፡ ህጉ የማንንም ኢትዮጵያዊ ምጣኔ ሀብታዊ አቅም ያላገናዘበ፣በአሰራር ውጣ ውረድ የተበተበና በዘፈቀደ እንዲወጣ የተደረገ ይመስላል ያሉት አባላቱ በተለይ የመንግስት ሠራተኞችን ከጨዋታ ውጭ ያደረገ ነው ብለዋል፡፡
አዲሱ የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ከብአዴን እየኮበለለ የሚጠፋውንና ለአሸባሪዎች መጠቀሚያ እየዋለ ነው ያሉትን ሃይል እንቅስቃሴ ለመግታት እርምጃ መውሰድ መጀመራቸውንም የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ።
በአማራ ክልል የሚገኙ ወጣቶችና የብአዴን አባላት ” ብአዴን የህወሀት በቅሎ መሆኑ ያብቃ” በማለት ጥያቄዎችን እያነሱ ነው።
በክልሉ ውስጥ የተንሰራፋው ሙስና፣ የመልካም አስተዳደር እጦትና አፈና መባባስ አባላቱን ለተስፋ መቁረጥ መዳረጉንም ወጣቶች ይናገራሉ።

የመረጃ ነፃነት?

የመረጃ ነፃነት?

(ይድነቃቸው ከበደ)
freedomof info



‹‹ ሕዝቡ እኔ ማን እንደሆንሁ ይላል ? ›› በማለት እየሱስ ክርስቶስ መረጃ ይጠይቃል ፤ ደቀመዛምርቶችም ስለሱ የተባለውን አንድም ሳያስቀሩ ይነግሩታል፡፡ እሱም መልሱ እንዲህ ይላቸዋል ‹‹ እናንተስ እኔ ማን እንደሆንሁ ትላላችሁ ? ››አላቸው ፡፡ እነሱም መለሱለት፡፡ ሙሉ ታሪኩ ሉቃስ 9ቁ 18 ላይ ይገኛል ፡፡
መረጃ አይናቅም አይደነቅም ማለት እንዲህ ነው፡፡ በመሰረቱ ክርስቶስ ሰዎች ስለሱ ምን እንዳሉ ብቻ ሳይሆን ምን እያሰብ እንደነበር የሚያውቅ አምላክ ነው፡፡ ግን መጠየቅ እና መመለስ አሳብን መግለፅ የሰው ልጅ ተፈጥሯዊ ባህሪ ነው፡፡ ለዚህም ነው ክርስቶ እንደሰው በምድር በተመላለሰበት ወቅት  መረጃ ይጠይቅ የነበረው እሱም ስለራሱ መረጃ ይሰጥ የነበረው፡፡ እርግጥ ነው ክርስቶስ ይህን ሲጠይቅ የራሱ ምክንያት አለው፡፡
በመሆኑም ሃሳብ መግለፅ ተፍጥራዊ መብት ነው ወደሚለው ዓለም አቀፍ ስምምነት በመደረሱ የመናገር ሃሳብን የመግለፅ ነፃነት የዲሞክራሲ ዋና የድም ስር ነው የተባለው፡፡ ስለዚህም ተሰባስቦ መቃወም እንዲሁም መደገፍ ፣ አንድ ሰው የሚመስለውን ሃሳብ በፈለገው መንገድ መግለፅ፣ የመምረጥና የመመረጥ፣ መንግስትን የመተቸት፣ በራስ ፍቃድ የመናገረ እና ያለመናገር ፣ በዓልንና አይማኖትን መከተልና ማስፋፋት እንዲሁም ህግ ለሁሉም የሚሰራ ስለመሆኑ መረጋገጥ እና የመሳሰሉት ሁሉ ተግባራዊ የሚሆነው ተአቅቦ ያልተደረገበት የመናገርና የመረጃ መብት ልውውጥ ተግባሪዊ ሲሆን ብቻ ነው፡፡
ለመደርደሪያነት የዚህን ያኸል ከተባለ ወደ ዋናው ጉዳይ አስፈቅደን ሳይሆን ፈቅደን እንገባለን፡፡ ያነሳነው አሳብ ‹‹ መረጃ ›› እንደመሆኑ መጠን ያለማንም ጣልቃ ገብነት ተፍጥሯዊ መብታችን በፈለግነውና በፈቀድነው መንገድ እንገልፃለን፡፡ እኛ ስል ለመረጃ ነፃነት የቆምነው ሁላችንም ማለቴ ነው፡፡
ሰው በመናገሩ አና በመፃፉ ብቻ ለእስር እና ለስደት የሚዳረግበት አገር በዋነኝነት ከሚጠቀሱት ውስጥ ኢትዮጵያ አንዶ ናት፡፡ ነገር ግን ማንኛውም ሰው ያለማንም ጣልቃ ገብነት የአመለካከት እና ሐሳብን በነፃ የመያዝና በማንኛውም የማሰራጫ ዘዴ በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጪ የመግለፅ ነፃነት አለው፡፡የሚለው በኢትዮጵያ ህገመንግስቱ አንቀፅ 29 ተፅፎ ይገኛል፡፡ በእርግጥ ይህ መብት ገደብ ሊጣልበት እንደሚችል በህገ መንግስቱ ላይ ተገልፆ የተቀመጠ ሲሆን ገደብ ግን መሠረታዊ የሆነውን መረጃን የመስጠት እና የማግኘት እንዲሁም አስተሳሰብ ላይ ወይም አመለካከት ላይ ውጤት እንደማይኖረው በህገመንግስቱ ተገልፆ ይገኛል፡፡
ይሁን እንጂ አሳብን በነፃ ማሰብና ማንሸራሸር በአገራችን ወቅታዊ ሁኔታ እጅግ አዳጋች ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡ አልፎ ተርፎ በአስተሳሰብ ወይም በአመለካከት ላይ ተፅኖ እስከመፍጠር ተደርሶኦል ፡፡ ነገር ግን እንዲህ አይነቱ ሁኔታ ለህግም ሆነ ለሞራል ተቃራኒ እንደመሆኑ መጠን የፈጀውን ፈጅቶ ወደነበረበት መመለሱ የማይቀር ሃቅ ነው፡፡ ነፃ አሳብ የሚንሸራሸርባቸው ነፃ ጋዜጦችና መፅሔቶች ምን ያህል አሉ ? ያሉት ጋዜጦች እና መፅሔቶች እየደረሰባቸው ያለው ማስፈራሪያና ዛቻ ደረጃው ምን ያኸል ደርሶአል የሚለውን መመልከት ተገቢ ነው፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆነው በቅርቡ በወጣው አዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ አክራሪነትና ፅፈኝነት የሚያበረታቱና የሚያሰራጩ በማለት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ለህዝቡ ተገቢውን መረጃ እያስተላለፉ ያሉ የእትመት ውጤቶችን ከገቢያ ለማውጣትና ፈርጆ ለመክሰስ እየተደረገ ያለው ዝግጅት ሌላው ማሳያ ነው፡፡ጋዜጠኞችን በማሰቃየት፣በማሰር እና እንዲሰደዱ በማደረግ ኢትዮጵያ በዓለም ላይ በሁለተኝነት ደረጃ ላይ ትገኛለች ፡፡መንግስትን ተችቶ የፃፈና ፁሁፉ የወጣበት ጋዜጣ ወይም መፅሔት ጨምሮ ሁሉም ለእስር የሚዳረግበት ወይም አደገኛ ዛቻና መስጠንቀቂያ የሚሰጥበት ደረጃ ላይ ተደርሷል፡፡
በዲሞክራሳዊ ሥርዓተ ዜጎች የሚኖሩት ግልፅ በሆነ የሃሳብ ልውውጥ ነው፡፡ የትኛውም አይነት ሃሳብ ከማንም ሊመጣ ይችላል ቁም ነገሩ መሆን ያለበት የሚመጣው ሃሳብ የሚመከተው በምንድነው የሚለው ነው፡፡ ለነፃ ንግግር ችግር የተሻለው መንገድ የበለጠ ነፃ ንግግር ነው፤ በመናገር መብት ላይ የሚደረግ ማናቸውም ተፅእኖ ሲውል ሲያድር በእያንዳንዱ ግለሰብ የመናገር መብት ላይ ስጋት ሊያስከትል ይችላል፡፡ለዚህም ነው ወደነበረበት መመለሱ የማይቀር ነው ለማለት የሚያስደፍረው፡፡ምክንያቱ ደግሞ ማንም ሰው በስጋት ውስጥ መኖርን ስለማይፈልግ ነው፡፡
በመሆኑም በአገራችን እየከሰመ ያለው ሃሳብን በነፃ የመግልፅ እና መረጃ የማግኘት መብት በገዥው መንግስት መልካም ፍቃድ ላይ የተመሠረት ወደመሆን ደረጃ ተሸጋግሯል፡፡ለዚህም እንደማሳያ ከሰሞኑ የህዝብ ሳይሆን የገዥው መንግስት አንደበት በሆነው በኢቲቪ  በተላለፈው የዘጋቢ ፊልም ግለሰቦችም ሆነ በአገር ውስጥ ያሉ የተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለይ ሰማያዊ እና አንድነት ፓርቲ ለኢሳት መረጃ ከመስጠት እንዲቆጠቡ ምክር መሰል ማስጠንቀቂያ ተላልፏል፡፡
ለዚህም እንደምክንያት የቀረበው ኢሳት የተባለው የመገናኛ ብዙሃን በሽብርተኛ ድርጅት የሚደገፍ ነው የሚል ምክንያት ነው፡፡ ኢቲቪ በኢህአዴግ እንደሚደገፍ ሁሉ ኢሳት በማንም ሊደገፍ ይችላል፤ ቁም ነገር ሆኖ መታየት ያለበት ኢቲቪ ሆነም ኢሳት የሚያስተላልፉት መልዕክት ምንድነው ፡፡ በተጨማሪ መልዕክቱ ለህግም ሆነ ለሞራል ምን ያኸል ተቃራኒ ነው የሚለውን ነው፡፡ በተጨማሪ ኢቲቪ እንዲሁም ኢሳት በህግ መደመጥ እንዲሁም መሰማት የተከለከሉ የመገናኛ ብዙሃን ናቸው ወይ ተብሎ መጠየቅና መልስ ሊሰጥባቸው የሚገባ አሳቦች ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ ወደ መልሱ ስናመራ ኢቲቪ እንዲሁም ኢሳት በህግ የተከለኩ አይደሉም ዋንኛው እና አስፈላጊው ነገር ይሄ ነው ሌላው የህጉ ደጋፊ ሃሳብ ነው፡፡
በመሆኑም ከዚህ በኋላ የህግ ጉዳይ ሳይሆን የፍላጎት ምርጫ ነው የሚሆነው፡፡ የፈለጉትን መስማት እና ማዳመጥ እንዲሁም በፈለጉት የመገናኛ ብዙሃን መንገድ ሃሳብን መግለፅ እና መረጃን ማግኘት ግለሰብ ከሆነ እንደግለሰቡ፣ ተቋም እንደተቋም እንዲሁም ፓርቲ እንደ ፓርቲ የመምረጥ የራስ መብት ነው፡፡ ይህ ደግሞ አንዱ የዲሞክራሲ መገለጫ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ከኢቲቪ ኢሳት ከአዲስ ዘመን አዲስ አድማስ የዝወትር ፍላጎታቸው ለሆነ እንዲሁም በተመሳሳይ ከኢሳት ኢቲቪ ከአዲስ አድማስ አዲስ ዘመን ለመረጡ ምርጫቸውን ማክበረ ነው፡፡
ሌላው እና አሳሳቢ ሊሆን የሚገባው ሰው የመረጠውን መስማትና ማዳመጥ እንዲሁም ማንበብ መብቱ እንደጠጠበቀ ሆኖ ግለሰበ ወይም ተቋም ሃሳቡን እንዴት የመግለፅ መብት እና ግዴታ አለበት የሚለው ነው፡፡ ይህን በተመለከተ ተቋም ወይም ግለሰብ ሃሳብን ወይም መረጃን በማንኛውም መንገድ የመገልፅ ሙሉ መበት በህግ የተጠበቀ ነው ፡፡እንዲኹም የዚህ መብት ተቃራኒ የሆኑ ማናቸውም ነገሮች ተቀባይነት እንደሌላቸው በህገመንግስቱ ተደንግጎ ይገኛል፡፡ በዚህም መሰረት በኢሳት ሆነ በማናቸውም የመገናኛ ብዙሃን ሃሳብን መግለፅ እና መረጃን መስጠጥ በራሱ ወንጀል ወይም ጥፋት አይደለም ይህ የሆነው ደግሞ መብት ከመሆኑ አንፃር ነው፡፡
yidnekachew
ይድነቃቸው ከበደ
ከዚህ ጋር ተያይዞ መታየት ያለበት ሃሳብን በመግለፅ እና መረጃን በመስጠት ዙሪያ ግዴታ ሊያመጣ የሚችለው ምንድነው የሚለው ነው፡፡ ግለሰቡ ወይንም ተቋሙ በግልፅ በህግ የተከለከለ መረጃ ወይም ሃሳብ የገለፀ እንደሆነ ግዴታው ተጠያቂነትን ስለሚያመጣ በህጉ መሠረት ተጠያቂ ይሆናል፡፡ ይህ የህግ ተጠያቂነት አዱላዊነት የሌለበት ለሁሉም በሁሉም ቦታ እኩል የሚሰራ ነው፡፡ ይህም ማለት በህግ የሚያስጠይቅ ንግግር በኢሳትም ሆነ በኢቲቪ እንዲሁም በቢቢሲ ያደረግ በህግ ከመጠየቅ ንግግር ያደረገበት የብዙሃን መገኛኛ ሊታደገው አይችልም እንደማለት ነው፡፡
በመሆኑም በኢሳት ሃሳብን መግለፅ  እንዲሁም መረጃ መስጠት አልፈልግም ማለት መብት ነው፡፡ ነገር ግን በኢሳት አሳባችሁን አትግለፁ መረጃም አትስጡ ማለት ከፍላጎት የመነጨ ሃሳብ ብቻ ሳይሆን የለየለት የእብሪት ተግባር ነው፡፡ እንዲህ አይነቱ አሰፋሪ ምኞት እና ተግባር የሕግና የዲሞክራሲያዊ መብት ካለማወቅ የሚመነጭ አስተሳሰብ ብቻ ሳይሆን ተምሮ ያለመለወጥ ልክፍትም ጭምር ነው! በተለይ በመንግስት ደረጃ ሲታሰብ  እጅግ በጣም ያሳፍራል፡፡